ግብርናችንንለማዘመን፤ዶክተር መላኩ ወረደ፣ የብዝሀ ህይወታችን ባለዉለታ ሲታወሱ

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሑፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

ዶክተር መላኩ ወረደ፣ የብዝሀ ህይወታችን ባለዉለታ ሲታወሱ

ብዝሀ ህይወት (biodiversity) በምድራችን በሚገኙ ህይወት ባላቸዉ ፍጡራን መካከል ያለዉን ልዩነቶችን ያሳየናል፡፡ በዚሁ መሰረት የብዝሀ ዘር ጥናት በተለያዩ ዕፅዋት፣ እንስሳት እና ረቂቅ ህዋሳት መካከል ያለዉን ልዩነት በሳይንሳዊ መንገድ የምንፈትሽበትን መንገድ ያስችለና፡፡ ቀደም ባለዉ ቫቪሎቭ ባለዉለታችን በሚለዉ ብሎጌ ኢትዮጵያ ቁልፍ ለሆኑ ሰብሎች መገኛ እንደሆነች ለማሳየት ምክሬአለሁ፡፡

ምሥሉ የሚያሳየዉ በተለምዶ የቫቪሎቭ የዝርያዎች ወይም የዕፅዋት መገኛ ማዕከላት ሲሆኑ እነርሱም (1) ሜክሲኮ-ጉቴማላ፣ (2) ፔሩ-ኢኳዶር-ቦሊቪያ፣ (2A) ደቡባዊ ቺሌ፣ (2B) ደቡባዊ ብራዚል፣ (3) ሜዲቴራኒያን፣ (4) መካከለኛዉ ምሥራቅ፣ (5) ኢትዮጵያ፣ (6) መካከለኛዉ ኤሲያ፣ (7) ሕንድ እና በርማ፣ (7A) ሲያም-ማላያ-ጃቫ እና (8) ቻይናና ኮሪያ ናቸዉ።

ኢትዮጵያም ለጤፍ፣ ቡና፣ ኑግ፣ ሰሊጥ፣ ዳጉሣ፣ የጉሎ ፍሬ፣ እንሰት፣ ጌሾ፣ ጫት፣ ኮሶ እና የመሳሰሉት መገኛ ወይም መነሻ ተብላ ትገመታለች፡፡ ይህም ማለት በሀገራችን በርካታ ከላይ የተጠቀሱት ሰብሎች ዝርያዎች ይገኛሉ ማለት ነው፡፡ እነዚህን የተለያዩ ሰብሎች ዝርያዎች አሰባስቦ፣ በተገቢ ሁኔታ አስቀምጦና ጥናት ማድረግ አስፈላጊ ነዉ፡፡ ምክንያቱም ለተለያዩ ጥናቶች የሚያገለግሉ ዝርያዎች ከነዚህ ናሙናዎች ዉስጥ ሊገኙ ስለሚችሉ ነዉ፡፡

በዚህ ጉዳይ በሀገራችን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉት ዶክተር መላኩ ወረደ ናቸዉ ብል ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡ ዶክተር መላኩ በወቅቱ PGRC/E Plant Genetic Center of Ethiopia (የአሁኑን EBI የኢትዮጵያ ብዝሀ ዘር ኢንስቲትዩት) የተባለዉን ተቋም በዳይክሬትነት እ አ አ ከ1979 እስከ 1993 ለ14 ዓመታት በመምራት ባገለገሉበት ወቅት ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ የተለያዩ ሰብሎች ዝርያዎች እንዲሰባሰቡና በተገቢ ሁኔታ እንዲቀመጡ ለማድረግ ችለዋል፡፡ ይህም ማለት አስፈላጊ የሆነ የሙቀት መጠንና ሌሎች አስፈላጊ ሁኔታዎችን ባገናዘበ መልክ ማለት ነዉ፡፡

ዶክተር መላኩ ወረደ እኚህ ነበሩ፡፡ ምንጭ፤  https://rightlivelihood.org/the-change-makers/find-a-laureate/melaku-worede/

ከዚህ በተጨማሪ ዶክተር መላኩ የሚታወቁበት ገበሬዎችን ያማከለ የብዝሀ ዘር ጥበቃ እንዲደረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉ ከመሆናቸዉም በላይ ይኸዉ ገበሬዎችን ያሳተፈዉ መንገድ ብዝሀ ዘርን በዘላቁነት ለመንከካበብ እንደ ግንባር ቀደም የመፍትሔ አካል እንዲሆን ያደረጉ እና ይህንንም በዓላም አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ እንዲሆን ለማደረግ ያስቻሉ ናቸዉ፡፡ ይህንኑ በሥልጠና መልክ በተለያዩ ሀገራት በመስጠት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡

ዶክተር መላኩ ወረደ በርካታ  ሽልማቶችና እዉቅናቸዎች የተበረከቱላቸዉ ሲሆን ከነዚህ ዉስጥ ሁለቱ፤ 1ኛ) እ አ አ በ1989 የተሰጣቸዉና ዘ ራይት ላይቪሊሁድ (The Right Livelihood) ሽልማት ወይም እንደ አማራጭ የኖብል ሽልማት የሚታወቀዉ ሲሆን የተሰጣቸዉም የኢትዮጵያን በርካታ ብዝሀ ዘር በተገቢዉ ሁኔታ ለማስጠበቅ ምርጥ ማዕከላት እንዲገነቡ በማስቻላቸዉ ነዉ፡፡ ይኸዉ ሽልማት ሎሬት የሚባል የክብር ስም እንዲሰጣቸዉ አስችሏል፡፡ እንደሚታወቀዉ ሁሉ ቢሊሃሪዚያ ተብሎ የሚጠራዉን አደገኛ በሽታ በቀላል ወጪ ለመከላከል እንዶድን በጥቅም ላይ ያዋሉት ፕሮፌሰር አክሊሉ ለማና ዶክተር ዶክተር ለገሠ ወልደ ዮሀንስም ይህንኑ የላይቪሊሁድ ሽልማት በጋራ ማሸነፋቸዉ ይታወሳል፡፡

2ኛ) እ አ አ በ2008 ላደረጉት ከፍተኛ ዓለም አቀፍ አስተዋፅዖ ከኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት ተሸልመዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ካበረከቷቸዉ አስተዋጽዎች መካከል ዋነኞቹ በዓለም አቀፍ የምግብና እርሻ ድርጅት የዕፅዋት ብዝሀ ዘር የሚመለከት ኮምሽን ሊቀመንበር፣ የዕፅዋት ብዝሀ ዘር ኢንስቲትዩት የቦርድ አባልና በተለያዩ ተቋማት የሰጧቸዉ ሥልጠናዎችን ያካትታል፡፡

ሕትመትን በተመለከተ ዶክተር መላኩ የተለያዩ ጽሁፎችን ያሳተሙ ሲሆን ከነዚህ መካከል የሚከተሉት መጽሐፍት ይገኙባቸዋል፡፡

  • Plant genetic Resources of Ethiopia  እ አ አ በ1991 የታተመ
  • Seeds of survival እ አ አ በ1999 የታተመ
  • The race to save Africa’s seed እ አ አ በ2005 የታተመ

በዶክተር መላኩ ወረደ እና ባልደረቦቹ የታተመዉ መጽሐፍ የፊት ሽፋን

ከዚህም በተጨማሪ የዶክተር መላኩን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እዉቅና ለመስጠት ጊያ ፋዉንዴሽን የሚባል ተቋም በዶክተር መላኩ ሥራ ላይ ያተኮረ Seeds of Justice : in the hands of Farmers የተባለ 40 ደቂቃ የሚፈጅ ዶኩመንታሪ ፊልም እ አ አ በ2015 አዘጋጅቷል፡፡

እኚህ የብዝሀ ህይወታችንን በተገቢዉ ሁኔታ በማሰባሰብና በማስጠበቅ ከፍተኛ አስተጽኦ ያደረጉልን ከሀገራችንም አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ እዉቅናን ያተረፉ ምሁር ከሁለት ቀናት በፊት ሐምሌ 26 ቀን 2015 ዓ.ም. በተወለዱ በ87 ዓመታቸዉ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዉናል፡፡ ለቤተሰቦቻቸዉ፣ ጓደኞቻቸዉ እና የሥራ ባልደረቦቻቸዉ መጽናናትን እመኛለሁ፡፡

ወደፊት በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ሐምሌ 26 ቀን 2015 ዓ.ም. (August 2, 2023)

One thought on “ግብርናችንንለማዘመን፤ዶክተር መላኩ ወረደ፣ የብዝሀ ህይወታችን ባለዉለታ ሲታወሱ

  1. እናመስናለን ዶ/ር ኃላፍ መሆናችንን አዉቀን አሻራችንን በትውልዱ ልቡና እናሳርፍ የሚል መልክት የያዘ ይመስላል!

    Like

አስተያየት ያስቀምጡ