ግብርናችንን ለማዘመን፤ ቫቪሎቭ ባለዉለታችን

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ቫቪሎቭ ባለዉለታችን

ኒኮላይ ቫቪሎቭ እ.ኤ.አ. ኖቨምበር 25፣ 1987 ተወልዶ በ1943 ከዚህ ዓለም በሞት የተለየ የሩሲያ ሣይንቲስት ነበር። በሕይወት ዘመኑ ከሠራቸው ሥራዎች ሁሉ በዓለም የታወቀበት የሰብሎች ወይም የተክል መገኛ ሥፍራዎችን ለይቶ በማስቀመጡ ነዉ። እነዚህ የሰብል መገኛ ሥፍራዎች ስምንት ዋና ማዕከላት ሲሆኑ ከንዑስ ማዕከላት ጋር አሥር ይሆናሉ። ቫቪሎቭ ባለዉለታችን ነዉ ያልኩትም ኢትዮጵያን አንድ ዋና የሰብል መገኛ ማዕከል አድርጎ በመሰየሙ ይህንንም ለዓለም በማስተዋወቁ ነዉ። ከታች በምሥሉ እንደሚታየዉ ከዚህ ሥራዉ በተጨማሪ ቫቪሎቨ በሀገሩ በርካታ የምርምር ማዕከላትን በማቋቋም ይታወቃል።

ምሥሉ የሚያሳየዉ በተለምዶ የቫቪሎቭ የዝርያዎች ወይም የዕፅዋት መገኛ ማዕከላት ሲሆኑ እነርሱም (1) ሜክሲኮ-ጉቴማላ፣ (2) ፔሩ-ኢኳዶር-ቦሊቪያ፣ (2A) ደቡባዊ ቺሌ፣ (2B) ደቡባዊ ብራዚል፣ (3) ሜዲቴራኒያን፣ (4) መካከለኛዉ ምሥራቅ፣ (5) ኢትዮጵያ፣ (6) መካከለኛዉ ኤሲያ፣ (7) ሕንድ እና በርማ፣ (7A) ሲያም-ማላያ-ጃቫ እና (8) ቻይናና ኮሪያ ናቸዉ።

ቫቪሎቭ ወዴት ተጓዘ? ቫቪሎቭ ከላይ የተጠቀሰት ሥፍራዎች የሰብሎች መገኛ ወይም መነሻ ናቸዉ ብሎ ከመሰየሙ በፊት ለ17 ዓመታት (እ.ኤ.አ. ከ1916 እስከ 1933) በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች መጠነ-ሰፊ ጉዞ አድርጓል። በዚህ ጉዞዉ በኤሲያ፣ አፍሪካና አሜሪካ የሚገኙ 50 ሀገሮችን የጎበኘ ሲሆን በርካታ ቁጥር ያላቸዉ የሰብል ዝርያዎችን ለመሰብሰብ ችሏል። አንዳንዶች እስከ 250 ሺህ የሚደርሱ ዝርያዎች በማሰባሰብ በሴንትስበርግ (በቀድሞ ስሟ ሌኒንግራድ) የዘር ማከማቻ እንዳስቀመጠ ይገመታሉ።

የቫቪሎቭ የኢትዮጵያ ጉዞ እንዴት ነበረ? ቫቪሎቭ እ.ኤ.አ. ዲሴምበር 1926 (የዛሬ 93 ዓመት) የኢትዮጵያ (በወቅቱ ወደምትጠራበት “አብሲኒያ”) ጉዞዉን ጀመረ። መረጃዎች እንደሚያሳዩት በጂቡቲ በኩል ወደ ኢትዮጵያ የገባ ሲሆን በጉዞዉ ያለፈባቸዉ ሥፍራዎች እንደ ቅደምተከተላቸዉ ድሬዳዋ፣ ሐረር፣ ፍቼ፣ አዲስ አበባ፣ አንኮበር፣ ደብረ ሊባኖስ፣ ጎንደር፣ አክሱም፣ አሥመራ፣ ምጽዋ ናቸዉ። ቫቪሎቭ ጉዞዉን የጨረሰዉም ከአራት ወራት በኋላ በአፕሪል 1927 ነዉ። ቫቪሎቭ አዲስ አበባ ሲደርስ ራስ ተፈሪ በክብር ተቀብለዉታል። በፌብሪዋሪ 7፣ 1927 ቫቪሎቭ ከአዲስ አበባ ወደ አንኮበር ጉዞወን ጀመረ። በዚህ ጉዞዉም 11 አባላት ያሉት የጦር መሣሪያ የታጠቁና ጦር የያዙ ሰዎች ሲከተሉት 12 በቅሎዎችም ነበሩት። ቫቪሎቭ በኢትዮጵያ በነበረዉ ጉዞዉ በሀገሪቱ ባለዉ የብዝሀ ሕይወት ዓይነትና ብዛት እጅግ እንደተደነቀ መረጃዎች ያሳያሉ።

ኢትዮጵያ መገኛ ወይም መነሻ የተባለችዉ ለየትኞቹ ሰብሎች ነወ? ጤፍ፣ ቡና፣ ኑግ፣ ሰሊጥ፣ ዳጉሣ፣ የጉሎ ፍሬ፣ እንሰት፣ ጌሾ፣ ጫት፣ ኮሶ እና የመሳሰሉት ናቸዉ።

ቫቪሎቭ ዕድሜዉ ለምን በአጭሩ ተቀጨ? ቫቪሎቭ የሞተዉ በ55 ዓመቱ በእስር ቤት ውስጥ ነዉ። ያገኘሁት መረጃ እንደሚያሳየዉ ለእስር ያበቃዉ ምክንያት በወቅቱ የሩሲያ መሪ ለነበሩት ቅርበት ካለዉ ሣይንቲስት ጋር መግባባት ባለመቻሉ ነዉ። በዚሁ መሠረት እ.ኤ.አ. ኦግስት 6፣ 1940 ከሥልጣኑ ተነሥቶ ወደ እስር ቤት ተወረወረ። በዓመቱ ጁላይ 19፣ 1941 የሞት ቅጣት ተፈረደበት። ይሁን እንጂ በጁን 23፣ 1942 የሞት ፍርዱ ወደ 20 ዓመት ቢቀየርለትም አንድ ዓመትም ሳይቆይ በጃንዋሪ 26፣ 1943 በታሰረበት እስር ቤት ዉስጥ ከዚህ ዓለም ተሰናበተ። የሞት መንስኤዉም ረሃብ እንደሆነ ይገመታል።

ቫቪሎቭ ያከማቸዉ ዘር እንዴት ከጥቃት ሊተርፍ ተረፈ? በሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ወቅት ወደ ሩብ ሚሊዮን የሚጠጋዉ ዘር ከጀርመን ወታደሮች ጥቃት ለመጠበቅ የመሥሪያ ቤቱ ሠራተኞች በተራ በመጠበቅ ከጥቃት ሊያድኑ ችለዋል። ምንም እንኳ የሚጠብቁት ዘር ነፍሳቸዉን ሊታደግ እንደሚችል ቢያዉቁም ይህን ብርቅዬ ዘር አንነካም ብለዉ በነበረዉ ከፍተኛ ረሃብ ምክንያት ዘጠኝ ጠባቂዎች በረሃብ ሊሞቱ ችለዋል።

ቫቪሎቭ ከሞተ በኋላ ምን ተፈጠረ? ቫቪሎቭ ከሞተ 12 ዓመታት በኋላ እ.ኤ.አ. በ1955 ክሱ ተነሳለት። በማስከተልም ቀድሞ የነበሩ የቫቪሎቭ ዝናና የተረፉ ሥራዎቹን መንግሥት በኦፊሲያል አወቀ። የሶቭየት ጀግናም ተባለ። በሴንትስበርግ የሚገገኘዉና በዋናነት በቫቪሎቭ የትሰበሰበዉ ትልቁ የብዝሀ ዘር መንከባከቢያ መሥሪያ ቤት የቫቪሎቭ ኢንሲቲትዩት ተብሎ ተሠየመ።

ማጠቃለያ፤ ከላይ በጥያቄና መልስ ለማሳየት እንደሞከርኩት ቫቪሎቭ ለአለማችን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረገ ሲሆን ሀገራችንንም በውጭዉ ዓለም በማስተዋወቅ ባለዉለታችን ነዉ። ምንም እንኳ የበለጠ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ በሚገኝበት ወቅት ወደ እስር ቤት ተወርዉሮ የሕይወቱ ፍጻሜ ሊሆን ቢችልምም የሀገሪቱ መሪ ሲቀየር በቫቪሎቭ የተበየነበት የዉሸት ፍርድ ተነስቶለትና የቀድሞ ዝናዉ ሊመለስለት ችሏል።

በሚቀጥለዉ በቸር ይግጠመን።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ሰኔ 27፤ 2011 ዓ.ም. (July 4, 2019)

One thought on “ግብርናችንን ለማዘመን፤ ቫቪሎቭ ባለዉለታችን

አስተያየት ያስቀምጡ