ግብርናችንን ለማዘመን፣ በምግብ ዋስትና ጥራትም ቢታከልበት

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። አነዚህ ጽሁፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

በምግብ ዋስትና ጥራትም ቢታከልበት

የምግብ ዋስትና በአራት ዋና ምሰሶዎች ይወከላል። አነሱም 1ኛ) የምግብ በበቂ መጠን መቅረብ፣ 2ኛ) በቂና ተመጣጣኝ ምግብ የመግዛት አቅም መኖር፣ 3ኛ) ተመጣጣኝና ተስማሚ የሆነ ምግብ የምንጠቀምበት ዕውቀት በበቂ ሁኔታ መኖር እና 4ኛ) በቂና ተመጣጣኝ ምግብ በዘላቂነት መኖር ናቸዉ። ስለዚህ የምግብ ዋስትና ተጠበቀ ስንል ከላይ የተገለጹትን አራት ነጥቦች ባገናዘበ መልክ መሆን ይገባዋል። ነገር ግን በአቅም ዉስንነት የተነሳ የኛንም ሀገር ጨምሮ በበርካታ በመልማት ላይ ባሉ ሀገራት ቅድሚያ የሚሰጠዉ በተራ ቁጥር አንድ ለተገለጸዉ ለምግብ አቅርቦት ነዉ።

ኢትዮጵያን ብቻ ብንመለከት የአለም የእርሻና የምግብ ድርጅት መረጃ እንደሚያሳየዉ አ.ኤ.አ. በ2016 ብቻ 1.5 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት የተለያዩ የእርሻ ዉጤቶችን ወደ ሀገር ዉስጥ አስገብታለች። ከነዚህ ውስጥ ከፍተኛዉን ድርሻ የሚይዙት የፓልም ዘይት 522.7 ሚሊዮን ዶላር፣ ስንዴና የስንዴ ዉጤቶች 305.5 ሚሊዮን ዶላር፣ ስኳር 260.6 ሚሊዮን ዶላር እና ሩዝ 201.7 ሚሊዮን ዶላር ናቸዉ። ነገር ግን በተመሣሣይ ዓመት ቡና፣ ሰሊጥንና የቁም ከብቶችን ጨምሮ ወደ ውጭ ከምትልካችዉ የእርሻ ዉጤቶች ሀገሪቷ ባጠቃላይ ያገኘችዉ 2.2 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነዉ። ይህ የሚያሳየዉ ከሰማኒያ ፐርሰንት በላይ ህዝቧ በእርሻ ቢተዳድርም ከዚህ ሴክተር የሚገኘዉ ምርት የሀገሪቷን የምግብ ፍላጎት እንደማያሟላ ነዉ።

ምንም እንኳ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ በመልማት ላይ ያሉ ሀገራት ህዝብ በእርሻ ቢተዳደርም ከዚህ ሴክተር የሚገኘዉ ምርት ለሀገር ዉስጥ ፍጆታ በቂ ባለመሆኑ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ሀገራት ከፍተኛ መጠን ያለው የተለያዩ የግብርና ዉጤቶች ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባትት ይገደዳሉ። ይህም ለከፍተኛ የዉጭ ምንዛሪ ይዳርጋቸዋል።

አንደሚታወቀው ሁሉ የምግብ አይነቶች ከሚሰጡት ጥቅም አንጻር በካርቦሃይድሬት፣ ፕሮቲን፣ ሜኒራል፣ ቫይታሚንና፣ ስብ ሥር ይመደባሉ። አነዚህ የምግብ አይነቶች በሰዉነታችን ዉስጥ አንዲገኙና በተፈለገዉ ሁኔታ ጥቅም ላይ አንዲዉሉ መመገብ ያለብን የምግብ አይነቶች አሉ። ነገር ግን አነዚህን በተፈለገዉ መጠንና ወቅት ካላገኘን በሰዉነታችን ላይ ጉዳት ይደርሳል። ለተለያየ በሽታም ይዳርገናል።

እያንዳንዱ ሀገር የራሱን ነባራዊ ሁኔታ ባጤነ መልኩ የብሔራዊ የምግብ አጠቃቀም መመሪያ ያዘጋጃል፣ ለተግባርነቱም አስፈላጊዉን ክትትል ያደርጋል። ይህም መመሪያ ጤናማ ዜጋን ለመፍጠር በሚያስችል መልኩ ይዘጋጃል። የተባበሩት መንግስታት የምግብና እና እርሻ ድርጅትም መመሪያዉን በማዘጋጀትና በማስፈጸም ረገድ ለአባል ሀገራት እገዛ ያደርጋል። እስካሁን ይህንን የምግብ አጠቃቀም መመሪያ ያዘጋጁት በአጠቃላይ 92 ሀገራት ሲሆኑ ከአፍሪካ ሰባት ብቻ ናቸዉ። እነርሱም ቤኒን፣ ኬኒያ፣ ናሚቢያ፣ ናይጄሪያ፣ ሲሼልስ፣ ሴራሊዮን እና ደቡብ አፍሪካ ናቸዉ። በጎጆ ቤት ምስል የቀረበዉ የቤኒኑ አጠር ያለ መመሪያ አንባቢያን በቀላሉ እንዲረዱት ተደርጎ የተሠራ ነዉ። ወደ 100 ገጽ የሚጠጋው የኬኒያዉ መመሪያ ደግም ሰፋ ቢልም የተሟላ መረጃ በዉስጡ ያካተተ ነው።

ብዙ ሀገራት የምግብ አጠቃቀም መመሪያቸዉን አንባቢያን በቀላሉ ሊረዱ በሚችሉበት መንገድ ያዘጋጃሉ። ከዚህ ዉስጥ ተመራጭ የሆነዉ በፒራሚድ መልክ የሚገለጸዉ ሲሆን ሰፋ ባለዉና የፒራሚዱ መሠረት የሚታዩት በበቂ መጠን መመገብ ያለብን የምግብ ዓይነቶች ናቸዉ። በተዋረድ የምግቡ ዓይነት የታየበት ስፋት ሲያንስ ከዚህ የምግብ ዓይነት የምንጠቀመዉ መጠንም እየቀነሰ ይመጣል ማለት ነዉ። በመሆኑም በላይኛውና ጠባቡ የፒራሚድ ጫፍ የሚዘረዘሩት የምግብ ዓይነቶች እጅግ በጥቂቱ የምንጠቀማቸዉ ናቸዉ። የብዙ ሀገራትን ልምድ ከግንዛቤ በማስገባት ከዚህ በታች ያሳየሁትን እንደ ምሳሌ መዉሰድ ይቻላል። በዚሁ መሠረት ቢቻል አትክልትና ፍራፍሬ በበቂ መጠን መመገብ ሲኖርብን የአልኮል መጠጥ ግን እጅግ ባነሰ መጠን መሆን ይገባዋል።

እነዚህ መመሪያዎች መመገብ የሚገባንን የምግብ ዓይነቶች ብቻ ሳይሆን ተዛማችነት ያላቸዉ መረጃዎችን ጭምር ያካትታሉ። ከነዚህ ዉስጥ በሰዉነታችን ክብደትና ቁመት ተመርኩዘን የምናሰላዉን ቦዲ ማስ ኢንዴክስ የሚባለዉን ይይዛሉ። ስለ ቦዲ ማስ ኢንዴክስና ጥቅሙ በሌላ ጽሁፍ እመጣበታለሁ።

ኢትዮጵያ ይህንን የምግብ አጠቃቀም መመሪያ በቅርቡ እንደምታዘጋጅ ተስፋ አደርጋለሁ። በዚህ መመሪያ የሚካተቱት ባብዘኛዉ ጊዜ ከሐኪሞቻችን ከሚለገሱን ምክሮች ጋር ተመሣሣይነት አላቸዉ። ልዩነቱ ይህንን መመሪያ ሳንታመምና ሐኪም ዘንድ ሳንሄድ ተግባራዊ ማድረግ ያለብን ስለሆነ ብቻ ነዉ።

ምንም እንኳ የተሟላ ባይሆንም የዚህ ብሎግ ጸሐፊ የሚከተሉትን ምክር ለመለገስ ይወዳል።

1ኛ) የሀገሪቱን የምግብ መመሪያ በቀላሉ መረዳት በሚቻል መልክ ማዘጋጀትና ለተጠቃሚዉ የሚዳረስበትን መንገድ ማመቻችት።

2ኛ) የውጭዉን የምግብ ሽፋን ሳናነሳ መጠቀም ቢቻል። ምክንያቱም ብዙ ሰብሎች በውጭዉ ሽፋናቸዉ ከፍተኛ የሆነ ንጥረ ነገር ይዘዋል። ስለዚህ የድንች ቅቅል ከነልጣጩ፣ የባቄላ አሹቅ ሳይፈለፈል፣ እንዲሁም ስንዴና ገብስ ሳንፈትግ መጠቅም ብንችል ይመረጣል።

3ኛ) የተሻለ የምግብም ሆነ የጤና አስተዋጽኦ ያላቸዉን ሰብሎች መምረጥ፣ ማምረትና በተጠቃሚዉ ዘንድ እንዲመለዱ ማድረግ። ለምሳሌ፣ በኢትዮጵያ በያመቱ ግማሽ ሚሊዮን ሄክታር በሚሆን መሬት ላይ በተለይም በሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ የሚመረትዉ ዳጉሳ በዉስጡ የያዘዉ ጠቃሚ ንጥረ ነገር ከፍተኛ ናቸዉ።  በተጨማሪም በምዕራብ የሀገራችን ክፍል ተወዳጅ የሆነዉ አንጮቴ በዉስጡ ከፍ ያለ ካልሼም፣ ፎስፎረስና የመሳሰሉትን አንደያዘ ጥናቶች ያስረዳሉ። ስለዚህ እነዚህንና ሌሎች ጥቅማቸዉ የሚታወቁትን ሰብሎች እንዲስፋፉ ማድረግ ጠቃሚ ነዉ።

4ኛ) እስካሁን ጥቅማቸዉ በሀገር ውስጥ ያልታወቁትን ቅጠላ ቅጠል፣ ሥራ ሥርና እንዲሁም ፍራፍሬዎች ጠቃሚና ጎጂ ጎናቸዉ ተጠንቶ በመጽሐፍ መልክ ቢዘጋጅ። አንዳንድ ተክሎች በሀገሪቱ በሰፊዉ ቢበቅሉም በተለያየ ምክንያት ጥቅም ላይ ልናዉላቸዉ አልቻልንም። ለምሳሌ ሞሎኪያ የሚባል በመካከለኛዉ አዋሽ በሚገኙ የጥጥ እርሻዎች ውስጥ በሰፊዉ የሚበቅል አረም ነበረ፤ አሁንም ያለ ይመስለኛል። ይህ ተክል በኛ ሀገር ለምግብነት ስለማንጠቅምበት እንደ ማንኛዉም አረም ነቅለን እንጥለዋለን። ነገር ግን እንደ ግብጽ ባሉ ሀገራት ይህ ተክል ተወዳጅ የሰዉ ምግብ ለመሥራት ይጠቅማል።

5ኛ) ገበሬዉም ሆነ የከተማ ነዋሪ የተለያዩ የአትክልትና ፍራፍሬ አይነቶች የሚያበቅሉበትና የሚመገቡበት ሁኔታ ቢመቻች። ተስማሚ የአየር ንብረትና ያፈር ሁኔታ ታይቶ ገበሬው ባለችዉ አነስተኛ የጓሮ እርሻ ከተሜዉም ባሉት ክፍት ቦታዎች ሊያመርቱ ይችላሉ። ይህ የከተማ እርሻ በአንዳንድ አገሮች የተለመደ ብቻ ሳይሆን በሰፊዉ በጥቅም ላይ የዋለ ነዉ። ወደ ስልሳ ሰባት ሺህ የሚጠጉት የግብርና ኢክስቴንሽን ሠራተኞች ካለባቸዉ የልማት ሥራ ጋር አጣምረዉ በጓሮ እርሻ ላይም ቢሳተፉ የበለጠ ዉጤታማ መሆን ይቻላል።

7ኛ) በምግባችንም ሆነ በትኩስ መጠጥ የምንጨምረዉን የስኳር መጠን በከፍተኛ መጠን መቀነስ።

6ኛ) የምግብ አሠራራችን በተለያዩ የፈጠራ ዉጤቶች እንዲበለጽግ ማድረግ። ለምሳሌ የወደፊቱ እንጄራችን ከጤፍ ብቻ ሳይሆን ለጤና ጠቃሚ ከሆኑ የተለያዩ የብርዕና አገዳ፣ ሥራ ሥር ወይም ሌላ ዓይነት ሰብል ጋር በማዋሃድ የሚዘጋጅበትንና እንደ አማራጭ የሚቀርብበት መንገድ ቢመቻች መልካም ይመስለኛል።

በሚቀጥለዉ በሌላ ርዕስ እንገናኝ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ግንቦት 13፤ 2011 ዓ.ም.