በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤
የአየር ንብረት ለውጥ — ምልክቶቹ
የአየር ንብረት ለዉጥ እጅግ አሳሳቢ እየሆነ ከመጣ ሰንበትበት ብሏል። አብዘኛዉ የዓለማችን ሕዝቦች የአየር ንብረት ለዉጥ በአጠቃላይ በኑሮዋቸዉ ላይ እያደረሰ ያለዉንና ወደፊትም ያደርሳል ተብሎ የሚጠበቀዉን እጅግ ስላሳሰባቸዉ በአስቸኳይ መፍትሔ እንዲፈልጉለት መንግሥታቸዉንና ዓለም አቀፍ ድርጅቶችን በየመድረኩ እየወተወቱ ይገኛሉ። የአንደኛ ተማሪዎች ሳይቀሩ የአየር ንብረት ለዉጥ መጥፎ ጠባሳ ጥሎብን ሳያልፍ እንታደገዉ እያሉ ነው። በዚህ የተነሣ ከአየር ንብረት ለዉጥ መንስኤዎች ጀምሮ ወደፊት ሊያጋጥም የሚችለዉን ክስተት የሚያካትት ሰፊ ጥናት ተካሂዷል። በሣይንስ የተደገፈ ትንበያም ተሰጧል።
የዛሬዉ ጽሁፌ የሚያተኩረዉ የአየር ንብረት ለዉጥ በአሁኑ ጊዜ እየተከሰተ እንደሆነና ወደፊትም ለመከሰቱ ፍንጭ እንዳለ የተወሰኑ አሀዞችን ለማሳየት ነዉ።
1ኛ) የአየርና የባህር ሙቀት መጨመር፤ የዓለማችን የአየር ሙቀት ከሰላሳ ዓመታት በኋላ ማለትም እ.ኤ.አ. በ2050 በአማካይ ሁለት ዲግሪ ሴንቲግሬድ እንደሚጨምር ይገመታል።ይህ አማካይ ሙቀት ነዉ እንጂ ባንዳንድ ሥፍራዎች የሚጨምረዉ የሙቀት መጠን ከዚህ በላይም ሊሆን ይችላል።

2ኛ) የዝናም እጥረት ወይም ድርቅ መባባስ፤ ባለፉት ሀምሳ ዓመታት በዝናም ማነስ የተነሳ በድርቅ የተጠቁ ሥፍራዎች ከዚያ በፊት ከነበሩት በእጥፍ ጨምረዋል።
3ኛ) የጎርፍ መብዛት፤ በአንዳንድ የዓለማችን ክፍሎች የዝናም መጠን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያንስ እንደሚጠበቀዉ ሁሉ በሌሎች አካባቢዎች ደግሞ እጅግ ከፍተኛ የሆነ ዝናምና እሱን ተከትሎ የሚመጣዉ ጎርፍ ይጠበቃል።
4ኛ) የግሪንሃዉስ ጋዝ (Greenhouse gas) መጠን መጨመር፤ ለጤና ጠንቅ የሆኑና ግሪንሃዉስ ጋዝ የሚል ስያሜ የተሰጣቸዉ ወደ ሰባት ይጠጋሉ። እነርሱም የዉሃ ትነት (H2O)፣ ካርቦንዳይኦክሳይድ (Carbon dioxide CO2)፣ ሚቴን (Methane CH4)፣ ኦዞን (Ozone O3)፣ ናይትረስ ኦክሳይድ (Nitrous oxide N2O)፣ ክሎሮፍሎሮካርቦንስ (Chlorofluorocarbons CFCs) እና ሃይድሮፍሎሮካርቦንስ (Hydrofluorocarbons HCFCs & HFCs) ናቸዉ። ከዚህ በፊት የተሠራ ጥናት እንደሚያሳየዉ ጥርት ባለ ሰማይ ቀን ከከባቢያችን አየር ዉስጥ የዉሃ ትነት 60% እጅ ሲይዝ ካርቦንዳዮክሳይድ 26%፣ ኦዞን 8% እና ሚቴን 6% በመያዝ ይከተላሉ። የግሪንሃዉስ ጋዞች ዋናዉ ባህሪያቸዉ ከከባቢያችን የአየር ክልል ወጥቶ የሚሄደዉን ሙቀት በማስቆም ተመልሶ ወደ መሬታችን እንዲደርስና ሙቀት እንዲሰጠን ማድረግ ነዉ። እነዚህ የግሪንሃዉስ ጋዞች በመጠኑ ሲሆኑ ከፍተኛ ጥቅም አላቸዉ፣ ያለእነርሱም በምድር ላይ መኖር አዳጋች ይሆን ነበር። ምክንያቱም የምድራችን ሙቀት በአማካይ ከዜሮ በታች 20 ድግሪ ሴንቲግሬድ አካባቢ ስለሚሆን ነዉ። ታዲያ እነዚህ እንደ ብርድ ልብስ ከላይ ሆነዉ መሬታችንን ባይሸፍኑልን ምን ይዉጠን ነበር። በሌላ በኩል የነዚህ ጋዞች በከባቢያችን ባለዉ አየር ሲከማቹ ከፍተኛ ጉዳት ያስከትላሉ። በአሁኑ ጊዜም በማስከተልም ላይ ይገኛሉ። ለወደፊቱ ደግሞ የከፋ ችግር እንዳያስከትሉ ከፍተኛ ሥጋት አለ። የዓለም ሜትሮሎጂካል ድርጅት ሪፖርት እንደሚያሳየዉ በአሁኑ ጊዜ ያለዉ የካርቦን ዳይኦክሳይድ መጠን 250 ዓመታት በፊት ከነበረዉ በ146% ከፍ ያለ ሲሆን ሚቴን በ257% እንዲሁም ናይትረስ ኦክሳይድ በ122% ብልጫ አሳይተዋል።
5ኛ) የበረዶ ክምችት መመናመን፤ በቀዝቃዛዉ የአለማችን ክፍል በተለይም በከፍተኛ ተራሮች ላይ ዓመቱን ሙሉ ተክማችቶ የሚገኝ ግሌሸር ተብሎ የሚጠራ በረዶ አለ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የዚህ ግሌሸር መጠን እየተመናመነ መጥቷል። ከዚህ በተጨማሪ በሰሜንና ደቡብ ዋልታ አካባቢ የሚገኙ የአርክቲክ እና የአንታርክቲክ ባህሮች የበረዶ መጠናቸዉ በከፍተኛ ደረጃ እየቀነሰ መጥቷል።
6ኛ) የባህር ወለል ከፍ ማለት፤ በብዙ የዓለማችን ክፍሎች በተለይም በባህርና ዉቅያኖስ ዳርቻ የሚኖሩ ሕዝቦች የባህር ወለል ቀድሞ ከነበረበት ከፍ ማለቱን ከተገነዘቡ ቆይተዋል። የቀድሞ ቀዬአቸዉንም ለቀዉ ከፍ ወዳሉ ሥፍራዎች ለመሄድ ተገደዋል። የባህር ወለል ከፍ ሊል የቻለዉ በሁለት ዋና ምክንያቶች ነዉ። አንደኛዉ ከላይ እንደተገለጸዉ ከፍ ባሉ ተራሮች ላይ ተከማችቶ የሚገኘዉ ግሌሸር መቅለጥና ከውሃዉ አካል ጋር መቀላቀል ሲሆን ሁለተኛዉ ደግሞ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚሞቀዉ የባህር አካል ሰፋ ያለ ሥፍራ ስለሚይዝ ወደ የብስ ስለሚስፋፋ ነዉ።
7ኛ) የባህር ዉሃ ወደ አሲዳማነት መቀየር፤ መረጃዎች እንደሚያሳዩት በአየር ውስጥ ካለው የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን ውስጥ 25% የሚሆነዉ ወደ ባህር ወይም ሌላ የዉሃ አካል ይገባል። ካርቦንዳይኦክሳይዱ ከውሃ ጋር ሲገናኝ ካርቦኒክ አሲድ ይፈጥራል። ከላይ እንደተገለጸዉ በአከባቢያችን ያለዉ የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን እየጨመረ ስለሆነ በዉሀ ወይም በባህር ዉስጥ የሚፈጠረዉ የአሲድ መጠንም በከፍተኛ ደረጃ ይጨመራል ማለት ነዉ። ይህም ዓሣን ጨምሮ በዉሃ ውስጥ ለሚኖሩ ፍጥረታት ጠንቅ ይሆናል ማለት ነዉ።
የነዚህ መጥፎ ከስተቶች አሳሳቢ አይደለም ትላላችሁን? ምድራችን አንድ ናት። ባንዱ ሀገር የደረሰዉ ክስተት ድንበር ሳይገድበዉ ወደ ሌላ ሀገር መሻገሩ አይቀርም። በርግጥ አንዳንድ ከስተቶች በአንድ አህጉር ብቻ ሊታዩ ይችላሉ። ይህ ግን ሁሌም እንደዛ ይሆናል ማለት አይደለም። ይህን በመገንዘብ ነዉ የዓለም መንግሥታት ለመፍትሔዉ በጋራ ለመሥራት ያቀዱት። በሚቀጥሉት ጽሁፎቼ የአየር ንብረት ለዉጥ በሰብሎቻችን፣ በእንስሳቶቻችን፣ በጤናችን፣ በዉኃችን ወዘተ ላይ የሚያደርሱትን እዘግባለሁ። በተጨማሪም ይህንን ለመታደግ መንግሥታዊም ሆነ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በማድረግ ላይ ያሉትን ጥረትና የተገኙ ዉጤቶችን በአጭሩ ለማሳየት እሞክራለሁ።
እስከዚያዉ በቸር ይግጠመን።
ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ሰኔ 3፤ 2011 ዓ.ም.












