ግብርናችንን ለማዘመን፤ የቆላ ስንዴን በመስኖ ያስተዋወቁን ፤ ዶ/ር ጀማል መሐመድ፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የቆላ ስንዴን በመስኖ ያስተዋወቁን ፤ ዶ/ር ጀማል መሐመድ፤ ክፍል 1

መስኖን በመጠቀም የቆላ ስንዴ ምርምርን በመካከለኛዉ አዋሽ ከመጀመራቸዉ ቀደም ብሎ ዶ/ር ጀማል መሐመድ በደጋዉ የሀገራችን ክፍል በስፋት በሚመረተዉ ስንዴ ምርምር ላይ ከፍ ያለ ልምድ አካብተዉ ነበር። የሶስተኛ ድግሬያቸዉን በጀርመን ሀገር ለመማር ዕድል ሲያገኙ ለዚሁ ማሟያ የሚሆን የምርምር ሥራቸዉን ከላይ በጠቀስኩት መስክ ለመሥራት አቀዱ፣ ለተግባራዊነቱም ተንቀሳቀሱ። ጊዜዉ እ አ አ በ 1985 የዛሬ 37 ዓመት መሆኑ ነዉ።

በዚሁ መሠረት የቆላ አየር ንብረት ወደ ሚወክለዉና የአዋሽ ወንዝን በመስኖ በመጠቀም የተለያዩ ሰብሎችን የሚያመርተውን የመልካ ወረር እርሻ ምርምር ማዕከል (ባሁኑ አጠራር የወረር ግብርና ምርምር ማዕከል)ን መረጡ። በወቅቱ የወረር ማዕከል የታወቀዉ በሰብሎች (ጥጥ፤ ኦቾሎኒ፤ ሰሊጥ)፣ በመስኖ፣ በአፈር እና በእንስሳት ምርምር ላይ ነበር። ከላይ የተጠቀሱት ሰብሎች ሞቃታማ የአየር ፀባይ ስለሚስማማቸዉ በዋናዉ የሰብል ወቅት በመስክ ላይ ምርምራቸዉ ይከናወናል። በአካባቢዉ ያሉ ስፋፊ የመንግሥት እርሻዎች ደግሞ ትኩረት አድርገዉ የሚሰሩት በጥጥ ላይ ነበር። በወቅቱ በመካከለኛው አዋሽ የነበሩት የወረር፣ የመልካ ሰዲ፣ የአሚባራ (የዕርዳታ ማስተባበሪይ ኮሚሽን የሚያስተዳድረዉ) እና ወደ 100 ኪሜ ራቅ ብሎ የሚገኘዉ የአሚባራ እርሻ የሚባሉ ሲሆን በኔ ግምት በድምሩ ወደ 10 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት ላይ ጥጥ ያበቅሉ ነበር። ቀስ በቀስ መሬቱ በጨዉ እየተበላ ከመቸገሩ በፊት የመልካ ሰዲ እርሻ የሙዝ እርሻም ነበረዉ። በታችኛዉ አዋሽ ሥር በዱብቲና አሳይታ አካባቢ የነበሩት እርሻዎችም ሰፋፊ የጥጥ እርሻዎች ነበሯቸዉ።

ሳላደንቀዉ የማላልፈዉ ነገር በዚያን ጊዜ የነበሩት የመንግሥት እርሻዎች ማሳዎቻቸው እጅግ ማራኪ መሆኑ ነዉ። ከጥጥ ለቀማ በስተቀር የተቀሩት የእርሻ ከንዋኔዎች ዘመናዊነትን የተላበሱ ነበር፤ ማለትም ሜካናዜሽን ይጠቀሙ ነበር ማለት ይቻላል። በእርሻ ምርምር ማዕከል የነበርን የሥራ ባልደረቦች በመንግሥት እርሻ በነበሩ ማሳዎች ጥራት እንቀና ነበር ብል የዋሸሁ አይመስለኝም። ምክንያቱም የእኛ ማሳዎች አንዳንዴ ዘመናዊነት ይጎድላቸዋል። ለዚሁም ዋናዉ መንስዔ እኛ ሙከራ የምናካሄደዉ እጅግ አነስተኛ በሆነ ማሳ ላይ ስለሆነ በሜካናዜሽን ልንሰራ ሁኔታዉ ሰለማይፈቅድልን ነዉ።

ሌላዉ አስደናቂ ነገር እያንዳንዱ የመንግሥት እርሻ የማሳ ኃላፊ ነበረዉ። ይኸ ኃላፊ ያለመታከት ማሳዉን በሞተር ብስክሌት ማየት የቀን ሥራዉ ብቻ ሳይሆን የሰዓታት ተግባሩ ነበር። ማሳዎቹ የመስኖ ውሃ እጥረትም ሆነ ብዛት ካለበት በቅርበት ያያል፣ ለመፍትሔውም በፍጥነት ይንቀሳቀሳል። ከሁሉም በላይ ከፍተኛ ትኩረት የሚደረገዉ በተባይ ላይ ነው። የጥጥ ተክል በተለይ ጥጡን የያዘዉ እምቡጥ በከፍተኛ ደረጃ በተባይ ይጠቃል። እንደ ቦል ወርም (boll worm) ጥጥን በተደጋጋሚ የሚያጠቃ፣ ተመራማሪዉንም ሆነ የልማት ሰራተኛዉን የሚፈታተን እንዲሁም የልማት መሥሪያ ቤቱን ለከፍተኛ ወጪ የሚዳርግ ያለ አይመስለኝም። ምክንያቱም በአንድ የስብል ወቅት ብቻ በርካታ ርጭቶች ማድረግ ስለሚያስፈልግ ነዉ።

የምርምር ማዕከላችን እና የመንግሥት እርሻዎች በቅርበት እንሰራ ነበር። እርሻዎቻቸውንም የእኛ የተባይ ጥበቃ ክፍል ባልደረቦች በየጊዜዉ ይጎበኙ ነበር። ከማሳዎች በሚወሰዱ ናሙናዎች ላይ በመመርኮዝ ስለ ተባይ አመጣጥ ትንበያ ያደርጋሉ። ይህም ወቅታዊ ርጭት እንዲደረግ ይረዳል። ከዚህ በተጨማሪ በማዕከላችን የተዋቀረዉና እኔም የአግሮኖሚ ዘርፍን በመወከል አባል የሆንኩበት የብሔራዊ የጥጥ ምርምር ቡድን በመካከለኛዉም ሆነ በታችኛዉ አዋሽ በሚገኙ እርሻዎች ጉብኝትና ግምገማ ያደርግ ነበር።

የወረርን ነገር ስነሳ ስለ ቆላ ስንዴና የዶ/ር ጀማል አስተዋጽኦ የጀመርኩትን ዘነጋሁ። ታዲያ ነገሩ እንደዚህ ነዉ።

በከፍተኛ ሙቀት ምክንያት በመደበኛዉ የሰብል ወቅት በመካከለኛዉም ሆነ በታችኛው አዋሽ ስንዴን ለመዘራት አይቻለም። የዶ/ር (በወቅቱ አቶ) ጀማል ምርምር ዓላማም በመደበኛዉ የሰብል ወቅት ስንዴ ለመዝራት አይደለም። ዋናዉ የዶ/ር ጀማል ዓላማ በዋናው የሰብል ወቅት ጥጥ ከተዘራና ለቀማ ከተከናወነ በኋላ መሬቱ ታርሶና ለስልሶ ስንዴ ቢዘራ የሚቀጥለዉ ወቅት የጥጥ ማሳ ዝግጅት ከመድረሱ በፊት ስንዴ የሚታጨድበትን ሁኔታ ለማጥናት የተወጠነ ነዉ። ስለዚህ ዋናዉ ዓላማ ሁለት ሰብሎች በዓመት የሚመረቱበትን ሁኔታ ለማጥናት ነበር። በተለይ ደግሞ ስንዴ ከፍተኛ ሙቀት መቋቋም ስለማይችል አጠር ባለ ጊዜ የሚደርሱና ለአካባቢዉ የአየር ፀባይና አፈር ዓይነት የሚስማሙ የስንዴ ዝርያዎችን ለማግኘት ነበር።

በዚሁ መሠረት ስንዴን ባማከለ የተለያዩ የምርምር ፕሮጀክቶችን በመንደፍ ወደ ሥራ ገቡ። እ አ አ በ1985 የመጀመሪያ ዓመት የምርምር ሥራቸውን በማከናዉእን ላይ ሳሉ እኔም በዚያዉ ዓመት ከሀረማያ ዩኒቨርስቲ በባችለር ዲግሪ ተመርቄና በእርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት ተቀጥሬ የወረር ግብርና ማዕከልን ተቀላቀልኩ። በማዕከሉም የስንዴ አግሮኖሚስት በመሆን ከዶ/ር ጀማል ጋር በቅርበት እንድሰራ ተመደብኩ። ስለዚህ ጀማሪ ተመራማሪ በሚል ማዕረግ የዕለት ተዕለት ሥራዬ የስንዴ ምርምር መረጃዎች መሰብሰብ ነበር። ዶ/ር ጀማል የሥራ ፍቅር አስተምረዉኛል። በዚያ የወረር ሞቃታማ አየር ቀኑን ሙሉ ሚዳ ላይ ስንሰራ እንዉል ነበር። እንደኔ በደጋዉ የሀገራችን ክፍል ተወልዶ እና ላደገ የወረር ሀሩር ቀላል ፈተና አልነበረም።

በምርምሩ ዉጤት መሰረት ባጭር ጊዜ የሚደርሱና ክጥቅምት እስከ የካቲት ባለዉ ጊዜ ውስጥ ከማሳ ዝግጅት አንስቶ እስከ ዘር እና አጭዳ የሚደርሱ ዝርያዎች ሊገኙ ችለዋል። ከነዚህም ዉስጥ ብሉ ጄይ፣ ቼናብ 70 እና ፓቮን 76 የሚባሉ ዝርያዎች ትዝ ይሉኛል። ከዝርያ በተጨማሪ ተስማሚ የዘር ወቅት፣ የዘር መጠን፣ የመዝሪያ ርቀት፣ የማዳበሪያ ዓይነትና መጠን ወ ዘ ተ ላይ ምርምር እናካሄድ ነበር። ክዶ/ር ጀማል ጋር ያደረግነዉ ምርምርም በርካታ ግኝቶችን አስገኝቷል። በፒ ኤች ዲ ቴሲሳቸዉም ይህንኑ ዘግበዋል፤ በሳይንሳዊ መጽሔቶችም አሳትመዋል። የቴሲሳቸዉ ርዕስም ከዚህ የሚከተለዉ ነዉ። Potentials and Possibilities of Double Cropping Wheat After Cotton Under Irrigation in Awash Valley, Ethiopia. Justus-Liebig-Univertsitöät ; Giessen, Germany. 1989.

በአጠቃላይ እንደ ዶ/ር ጀማል ግምት ስንዴን ከጥጥ አስከትለን በመዝራት በአዋሽ ሸለቆ ብቻ እስከ 500 ሺህ ኩንታል ስንዴ ማምረት እንደሚቻል ነዉ። የስንዴዉ ተረፈ ምርት የሆነዉ ገለባዉና ጭዱም ደግሞ ለእንስሳት መኖነት ያገለግላል። ስለዚህ ስንዴ እና ጥጥን በማፈራረቅ በዓመት ሁለት ሰብል መዝራቱ ለሀገራችን ምግብ ዋስትና ከፍተኛ አስተዋ|ጽኦ ይኖረዋል በማለት ዶ/ር ጀማል የምርምር ሥራቸዉን ያጠናቅቃሉ።

ስለ ዶ/ር ጀማል የምጽፈው በዚህ አያበቃም። በክፍል ሁለት ዶ/ር ጀማል የተሳተፉባቸዉ ሌሎች የሥራ መስኮችና ከኔም ጋር በቅርቡ አብረን ልንሰራ ያቀድነውን የምርምር ፕሮጀክት አስነብባችኋለሁ።

እስከዛዉ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 15፣ 2015 ዓ.ም. (December 24, 2022)

ግብርናችንንለማዘመን፤የጤፉ መሐንዲስ ሲታወሱ

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የጤፉ መሐንዲስ፤ ዶ/ር ታረቀ በርሔ ሲታወሱ

የዛሬ ሶስት ዓመት ገደማ ማለትም በየካቲት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. (February 21, 2020) እና የካቲት 15 ቀን  2012 ዓ.ም. (February 23, 2020) በጻፍኳቸዉ ሁለት ብሎጎች በጤፍ ምርምር ፈር ቀዳጅ ሥራ ሰለሰሩት ዶ/ር ታረቀ በርሔ ጽፌ ነበር፡፡ በወቅቱ የጻፍኳቸዉ ብሎጎች በቀጥታ ለራሳቸዉ ካደረኩላቸዉ ቃለ መጠይቅ በመመርኮዝ ነበር፡፡

እኚህ ታላቅ ሰዉ በአሁኑ ጊዜ በአጠገባችን የሉም፡፡ በቅርቡ ከዚህ አለም በሞት ተለይተዉናል፡፡ ስለዚህ ከዚህ በፊት ስለ እሳቸዉ የጻፍኳቸውን ብሎግችና የዛሬዉን አንድ ላይ ባማጣመር ለዶ/ር ታረቀ ማስታውሻ ይሆን ዘንድ የሚከተለውን አቀርባለሁ፡፡

የካቲት 13 ቀን 2012 .. (February 21, 2020) ብሎጌ የተወሰደ

የዛሬዉ ጽሑፌ የሚያተኩረዉ ለጤፍ ምርምር ፈር ቀዳጅ ዉጤት ላገኙትና ይህም በጥቅም ላይ እንዲዉል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉት ስለ ዶክተር ታረቀ በርሔ ነዉ። እኚህን ከፍተኛ ተመራማሪ እኔ የጤፍ መሐንዲስ እላቸዋለሁ። ምክንያቱም ለምርምር እጅ አልሰጥ ብላ ባስቸገረችዉ ጤፍ ላይ ድል ሊቀዳጁ የቻሉ የመጀመሪያዉ ሰዉ በመሆናቸዉ ነዉ። ከእርሳቸዉ አስደናቂ ግኝት በፊት ጤፍን በማዳቀል ማሻሻል እንደማይቻል ነበር የሚታመነዉ። ምክንያቱም የጤፍ አበባ የሚከፈትበት ጊዜ ሊታወቅ ባለመቻሉ ነዉ። እንደዉም የጤፍ አበባ ፈጽሞ አይከፈትም የሚል ድምዳሜ ላይ ተደርሶ ነበር። ነገር ግን ዶክተር ታረቀ ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ የጤፍ አበባ ሊከፈት የሚችል መሆኑንና የማዳቀል ሥራዎችም በሰብሉ ላይ ማድረግ እንደሚቻል ለመጀመሪያ ጊዜ ያረጋገጡ ናቸዉ። የእሳቸዉ የጥናት ዉጤትም እንደሚያሳየዉ የጤፍ አበባ የሚከፈተዉ ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ 12 ሰዓት ተኩል በጠቅላላዉ ለ30 ደቂቃ ብቻ እንደሆነ ነዉ። ዶክተር ታረቀ ይህንን አስደናቂ ዉጤት ያገኙት የዛሬ 47 ዓመት በ1975 ነዉ።

ምስጋና ለዶ/ር ታረቀ ይሁንና የብሔራዊ ጤፍ ምርምር ፕሮግራም በማዳቀል ሥራ ላይ ትኩረት በማድረግ በርካታ የጤፍ ዝርያዎች እንዲጸድቁና ገበሬ ዘንድ እንዲደርሱ ለማድረግ ተችሏል፡፡ በአርሶ አደሩ ዘንድ አድናቆትን ያተረፉና ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችም ሊገኙ ችለዋል፡፡  በዚሁ በማዳቀል ሥራ እስካሁን ድረስ ወደ 30 የሚጠጉ የጤፍ ዝርያዎች የጸደቁ ሲሆን ዝርዝራቸዉንም ከዚህ በታች በቀረበዉ ሠንጠረዥ ማየት ይቻላል፡፡

በማዳቀል የተገኙ የተሻሻሉ የጤፍ ዝርያዎች በኢትዮጵያ

ተራ ቁየዝርያዉ ስምየጸደቀበት ዓመት    (እ አ አ) ተራ ቁየዝርያዉ ስምየጸደቀበት ዓመት    (እ አ አ)
1መናገሻ1982 15አቦላ2015
2መልኮ1982 16ንጉሥ2017
3ጊቤ1983 17ፍላጎት2017
4ጸደይ1984 18ተስፋ2017
5ዱከም1995 19ህብር2017
6ዝቋላ1995 20አረካ2017
7ቁንጮ2006 21ኤባ2019
8አማራጭ2006 22ቦራ2019
9ገመቺስ2006 23ዋሸራ2019
10ሲማዳ2009 24መና2019
11ላቀች2009 25አክሱማዊት2020
12ቦሰት2012 26ቢሾፍቱ2020
13ኮራ2014 27ታኩሳ2021
14ዳግም2016 28ቦኒ2021

ምንጭ፤ Assefa K, Chanyalew S, Tadele Z, Jifar H, Kebede W, Fikre T, Tolossa K, Genet Y. 2022. Tef Breeding. In: Assefa K, Chanyalew S, Girma D, Tadele Z. (eds.). Principles and Practices of Tef Improvement. Ethiopian Institute of Agricultural Research (EIAR) and Agricultural Transformation Institute (ATI), Addis Ababa, Ethiopia. pp. 95-125

ከዚህ አንጋፋ የጤፍ ምርምር ባለዉለታ ከሆኑት ከዶክተር ታረቀ በርሔ ጋር ያደረኩት ቃለ-መጠይቅ እነሆ።

መቼና የት ተወለዱ? የተወለድኩት ጃንዋሪ 22፣ 1943 ሲሆን በትግራይ ክልል ሥር በምትገኘዉና ከውቅሮ ከተማ 15 ኪ. ሜ. በምትርቀዉ አብርሃ በምትባለዉ መንደር ነው።.

ዩኒቨርስቲ ከመግባትዎ በፊት የት ተማሩ? የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቴን የተማርኩት አሥመራ በሚገኘዉ ሰባተኛዉ ቀን አድቬንቲስት ትምህርት ቤት ሲሆን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ደግሞ በጂማ የእርሻና ቴክኒክ ትምህርት ቤት አጠናቅቄአለሁ።

ዶክተር ታረቀ በርሄ (በስተግራ) ኖቮምበር 2011 ከጤፍ ተመራማሪዎች ጋር በደብረ ዘይት ምርምር ማዕከል የተነሱት ፎቶ።ሌሎች በምሥሉ የሚታዩት ከግራ ወደ ቀኝ፤ ዶክተር አንድረስስ ቢንደር፣ ዶክተር ኮሪና ኤስፌልድ፣ አቶ መንግሥቱ ደምሴ፣ ዶክተር ዘሪሁን ታደለ፣ ዶክተር ክበበዉ አሰፋና ዶክተር ገረመዉ ቡልቶሳ ናቸዉ።

የዩኒቨርሲቲ ትምህርትዎንስ የት ተማሩ? የባችለር ድግሬዬን በዕጽዋት ሣይንስ በቀድሞ አጠራሩ ኃይለ ሥላሤ ዩኒቨርስቲ የአለማያ እርሻ ኮሌጅ (በአሁኑ አጠራሩ፤ ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ) በ1969 አግኝቻለሁ። በመቀጠልም የማስትሬት ዲግሪዬን በአግሮኖሚ በአሜሪካ ፑልማን ከሚገኘዉ የዋሺንግተን ስቴት ዩኒቨርስቲ በ1974 ተቀብያለሁ። ፒ ኤች ዲ ደግሞ በአሜሪካ ከሚገኘዉ የኔብራስካ ዩኒቨርስቲ በፕላንት ቢሪዲንግና ጄኔቲክስ በ1981 ለማግኘት ችያለሁ።

ለበርካታ ዓመታት ከኢትዮጵያ ዉጭ በተለያዩ የኃላፊነት ሥፍራዎችና ሀገሮች እንደሠሩ ይታወቃል። ከዚህ ቀደም ብሎ በኢትዮጵያ ዉስጥስ ርተዋልን? አዎን፣ ለስምንት ዓመታት አገልግያለሁ። ከ1969 እስከ 1972 የጤፍ ተመራማሪ ሆኜ በደብረ ዘይት እርሻ ምርምር ማዕከል የሠራሁ ሲሆን ከ1974 እስከ 1977 ደግሞ በደብረዘይት ከነበረብኝ የጤፍ ምርምር በተጨማሪ በአለማያ እርሻ ኮሌጅ አስተምር ነበር።

ከኢትዮጵያ ውጭ በነበሩበት ወቅት በምን ላይ እንደተሳተፉና የኖሩበትን ሀገራት ቢገልጹልኝ፤

  • ከ1982 እስከ 1986 ድረስ INTSORMIL ለሚባለዉ ድርጅት የማሽላና ዳጉሣ ተመራማሪ ሆኜ ሱዳን ሀገር ዉስጥ ሠርቻለሁ።
  • ከ1987 እስከ 1989 ድረስ IITA ለሚባለው ዓለም አቀፍ ተቋም የበቆሎ ተመራማሪ ሆኜ በዛየር (በአሁኑ፤ የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ) አገልግያለሁ።
  • ከ1989 እስከ 1991 ድረስ Global 2000 ለሚባለዉ ድርጅት ከፍተኛ የበቆሎ አግሮኖሚስት : ሆኜ በዛምቢያ ሀገር ሠርቻለሁ።
  • ከ1991 እስከ 1996 ድረስ SG 2000 ለሚባለዉ ድርጅት ከፍተኛ የሰብል ሣይንቲስት ሆኜ ጋና ሀገር ሠርቻለሁ።
  • ከ1996 እስከ 2004 ድረስ SG 2000 ለሚባለዉ ድርጅት ጊኒያ በምትባለዉ ሀገር ዳይሬክቴር ሆኜ ሠርቻለሁ።
  • ከ2005 እስከ 2010 ድረስ ሳሳካዋ አፍሪካ በሚባለዉ ድርጅት የአህጉሩ የሩዝ ፕሮግራም ዳይሬክቴር ሆኜ የሰራሁ ሲሆን በዚህ ኃላፊነቴም የተሻሻሉ የሩዝ ቴክሎጂዎች ለኢትዮጵያ፣ ማሊ፣ ናይጄሪያ እና ኡጋንዳ እንዲደርሱ ለማድረግ ችያለሁ።
  • ክጃኑዋሪ እስከ ጁን 2011 ድረስ USAID/ARD/TASMOA በመባል ለተቀናጀ ድርጅት ተቀማጭነቴ ላይቤሪያ ሀገር ሆኖ የሩዝ ዘር ዳይሬክቴር በመሆን የተሻሻሉ የሩዝ ቴክሎጂዎች በአምራቹ ዘንድ እንዲሰርጹ ለማድረግ ችያለሁ።

የካቲት 15፣ 2012 ዓ.ም. (February 23, 2020) ብሎጌ የተወሰደ

ጥያቄ፤ ለበርካታ ዓመታት በተለያዩ ሀገራት ያደረጉትን ሥራ የዛሬ 10 ዓመት ካጠናቀቁ በኋላ ጡረታ ወጥተዉ ቁጭ አሉ?  ጡረታ ወጥቼ አላረፍኩም። በህይወት ዘመኔ ያካበትኩትን የሥራ ልምድ በመጠቀም የጤፍና የሩዝ ምርታማነት እንዲያድግ ኢትዮጵያ ዉስጥ ATA (Agricultural Transformation Agency ባሁኑ አጠራር ATI Agricultural Transformation Institute) ተብሎ በተቋቋመው ተቋም የሩዝ ቫሊዉ ቼይን ፕሮግራም ዳይሬክቴር ሆኜ ሠርቻለሁ።

የጤፍ ማዳቀል ሲነሣ የእርስዎ ስም ይነሳል። እንዲሁም የእርስዎ ስም ሲነሳ የጤፍ ስም ይነሳል። እስቲ በጤፍ ተመራማሪዎች ዘንድ ከፍተኛ አድናቆት ሰለተሰጥዎት ክስተት ቢያወሱኝበጤፍ ማዳቀል ላይ ሁለት አበይት እክሎች ነበሩ። የመጀመሪያዉ የጤፍ አበባ በማለዳ ብቻ ለአጭር ጊዜ እንደሚከፈት አለመታወቁ ነዉ። ሁለተኛዉ ደግሞ የጤፍ አበባ እጅግ አነስተኛ በመሆኑ ያለ አጉሊ መነጽር በአይናችን ብቻ የማዳቀል ሥራ ማከናወን አለመቻላችን ነዉ። ስለዚህ የተሳካ የጤፍ ማዳቀል ሥራ ለማከናወን ሦስት ነገሮች እንዲሟሉ ያስፈልጋል። እነዚህም 1ኛ) ከ30-40 እጥፍ የሚጎላ ባይኖኩላር ማይክሮስኮፕ፣ 2ኛ) እጅግ የተሳለና ቀጭን ፎርሴፕስ እና 3ኛ) የማይንቀጠቀጥ እጅ ናቸዉ። እኔ በጤፍም ሆነ በሌሎች ሰብሎች ተመራማሪዎች ዘንድ በሰፊዉ ልታወቅበት የቻልኩት የጤፍ አበባ በማለዳ ብቻ ለአጭር ጊዜ የሚከፈትበትን ጊዜ ለመጀመሪያ ጊዜ ማግኘቴ ብቻ ሳይሆን ይህንኑ ግኝት በመጠቀምና እንዲሁም የራሴን የዓላማ ጽናት በማከል ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳካ የጤፍ ማዳቀል ሥራ ለማከናወን በመቻሌ ነዉ።

እንዴት ይህንን አስደናቂ ግኝት ሊያገኙ ቻሉ? ለዚህ ግኝት ልበቃ የቻልኩት በሥራዬ ላይ በነበረኝ ከፍተኛ ትዕግሥትና የዓላማ ጽናት ሲሆን ወደምፈልገዉ ግብ ለመድረስም በነበረኝ ቁርጠኝነት ነዉ።

የጤፍ አበባ ይህንን ይመስላል። ሁለቱ ረዘም ያሉ ጸጉራም አካላት የሴቴዉን ወገን የሚወክሉት ስቲግማ ሲሆኑ አጠር ብለዉ ያሉት ሦስት ጥንዶች አንተር ተብለዉ የሚጠሩትን የወንዴዉን ፖለን የያዙ ናቸዉ። በቀኝ በኩል የሚታየዉ ስኬል ባር 1 ሚ ሜ ይወክላል። ፎቶ፣ ሬጉላ ብሎሽ፣ በርን ዩኒቨርስቲ፣ ስዊዘርላንድ።

በምርምር ዉጤትዎ በመመርኮዝ በርካታ ጽሑፎች አሳትመዋል። ነገር ግን ስለ ጤፍ አበባ አከፋፈትና እንዲሁም ማዳቀል ያገኙትን አስደናቂ ግኝት የት ነዉ ያሳተሙት? በርካታ ጽሑፎች ባሳትምም ከዚህ ግኝቴ ጋር በሚገናኝ ያሳተምኳቸዉ ጽሑፎች ከዚህ በታች ያሉት ናቸዉ።

  1. Berhe T. 1975. Breakthrough in tef breeding technique. Food and Agriculture Organization (FAO) Information Bulletin, Cereal Improvement and Production for Near East Project 12(3):11-13, FAO, Rome.
  2. Berhe T. 1976. Brighter prospects for improving Eragrostis tef by breeding. In: Proceedings on Evaluation of Seed Protein alternatives by Mutation Breeding, 5-9 May 1975, Vienna, Austria. International Atomic Energy Agency (IAEA), Vienna. pp. 129-135.
  3. Berhe T. 1976. The door is open for green evolution in tef. pp. 208-213. In: Proceedings of the Sixth Annual Research Seminar, 12-14 Nov 1975, Addis Ababa, Ethiopia. Institute of Agricultural Research (IAR), Addis Ababa.
  4. Addis Zemen Gazetta. 1975. ዓመት-ምህረቱን እንጂ የህትመቱን ቀን አላስታዉስም።

እ.ኤ.አ. ከኦክቶበር 22 እስክ 24፣ 2019 በቢሾፍቱ በተካሄደዉ ዓለም-አቀም የጤፍ ወርክሾፕ ላይ ዶክተር ታረቀ በርሄ ንግግር ሲያደርጉ ይታያል። ፎቶ፣ ዘሪሁን ታደለ

በርካታ ሽልማቶችና እዉቅና እንዳገኙ ይታወል። እስቲ ከነዚህ ዉስጥ ዋነኞቹን ቢገልጹልኝ፤ በዉጭ ሀገራትም ሆነ በአገር ዉስጥ የተሸለምኳቸዉና የተሰጠኝ እዉቅና በአራት ከፍሎ ማየት ይቻላል።

  1. ከአለማያ የእርሻ ኮሌጅ የእጽዋት ሣይንስ ተመራቂዎች መካከል የላቀ ዉጤት በማግኘቴ (በ1969)
  2. የዕውቅና ሠርቲፊኬት
  3. በ50ኛዉ ዓመት የአለማያ ዩኒቨርስቲ ምሥረታ በዓል (በ2005)
  4. በመጀመሪያዉ የአፍሪካ ሩዝ ኮንግረስ (በ2006)
  5. ከሣሣካዋ አፍሪካ በታዋቂዉ የአረንጓዴ አብዮት መሐንዲስ ዶክተር ኖሮማን ቦርሎግ እና በቀድሞዉ የአሜሪካ ፕሬዘዳንት ካርተር የተፈረመ (በ2006)
  6. የወርቅ ሜዳሊያና ሠርቲፊኬት የተሸለምኩበት
  7. በ40ኛዉ ዓመት የደብረ ዘይት ምርምር ማዕከል ምሥረታ በዓል (በ2005)
  8. በ50ኛው ዓመት የኢትዮጵያ እርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት ምሥረታ በዓል (በ2008)
  9. የክብር ዶክትሬት ከመቀሌ ዩኒቨርስቲ (በ2014)

ከኢትዮጵያዊያን ተመራማሪዎች መካከል እንደ ጀግና (hero) የሚቆጥሯቸዉን ሶስት ምሁራን ቢጠቅሱልኝ፤ በጤፍ ምርምር ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ናቸዉ ብዬ የምገምታቸዉ ዶክተር መላክ ኃይል መንገሻ፣ ዶክተር ሠይፉ ከተማ እና ዶክተር ክበበው አሰፋ ናቸዉ።

ካልዎት ረዥም ልምድ በመነሣት ለወደፊቱ የጤፍ ምርምር የሚለግሱት ምክር ባጭሩ ቢያካፍሉኝ፤ በህይወት ዘመኔ የጤፍ ምርት በሄክታር ከ80 እስከ 100 ኩንታል እንደሚደርስ ምኞቴ ነዉ።

ስለዶክተር ታረቀ በርሄ በሁለት ክፍል የቀረበዉ ጽሑፌ በዚህ ያበቃል። ከርሳቸዉ ረዥም የሥራ ልምድ በተለይም በጤፍ ምርምር ካበረከቱት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ብዙ የምንማረዉ ይኖራል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።

በመጨረሻም ለዶ/ር ታረቀ ቤተሰቦች እና ወዳጆች መጽናናትን እመኛለሁ፡፡

ወደፊት በሌላ ጽሁፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 12 ቀን 2015 ዓ.ም. (December 21, 2022)

ግብርናችንንለማዘመን፤ታዋቂዉ የጤፍ ታክሶኖሚስት፤ ታደሰ ኤባ፤ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ታዋቂዉ የጤፍ ተመራማሪና ታክሶኖሚስት፤ ታደሰ ኤባ፤ ክፍል 2

የክፍል 1 ጽሑፌ የጤፍ ተመራማሪ የነበሩት ዶ/ር ታደሰ ኤባ እ አ አ በ1975 ባሳትሙትና ‘Tef (Eragrostis tef) cultivar: Morphology and Classification’. Part II. Experiment Station Bulletin 66. Addis Ababa University, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia በሚለዉ መጽሐፋቸዉ ላይ ያጠነጠነ ነበር፡፡ በዚህ ድንቅ ሥራቸዉ ዶ/ር ታደሰ በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች የሚበቅሉ የጤፍ ዝርያዎችን በማሰባሰብና በጥልቀት በማጥናት እንዲሁም ዝርያዎቹ እርስ በርስ ያላቸዉን ቅርበትና ርቀት በሳይንሳዊ መንገድ በማጥናትና በመተንተን አቅርበዉልናል፡፡ በእኔ ግምት በእሳቸዉ ደረጃ የተለያዩ የጤፍ ዝርያዎችን አጥንቶና በተገቢዉ ምድብ ከፋፍሎ ያሳየን ሳይንቲስት አላየሁም፡፡ ስለዚህ የእሳቸዉ መጽሐፍ የጤፍ ዝሪያዎች ለመከፋፈል እንደ መመሪያ ሆኖ ያገለግለናል፡፡

ለዚሁ ድንቅ ስጦታቸዉ ማስታወሻ ይሆን ዘንድ በጤፍ ማሻሻያ ፕሮግራም ላይ ያለን ተመራማሪዎች ከሶስት ዓመት በፊት በብሔራዊ ዝሪያ አጽዳቂ ኮሚቴ የጸደቀልንን አዲስ የጤፍ ዝርያ ‘ኤባ’ ብለን ሰይመናዋል፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ይኸዉ የኤባ ዝርያ በአጭር ጊዜ ውስጥ በአምራቾች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያገኘ ሲሆን የዘር ጥያቄዉ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡

ለማስረጃም ያህል በሶስት ሥፍራዎች የኤባ ዝርያ በመስክ ላይ የነበረዉን እድገትና በፎቶግራፍ አስደግፌ ከዚህ በታች ለማሳየት እሞክራለሁ፡፡

ምንጃር ላይ ኤባ ዝርያን ከዘሩና ካደነቁት ሁለት አርሶ አደሮች ጋር ሆኜ የተነሳሁት እ እ አ ኦክቶበር 2021፡፡ ፎቶ አባተ በቀለ (ዶ/ር)

ሸንኮራ ላይ አንጋፋዉ የጤፍ ተመራማሪ ዶ/ር ክበበው አሰፋ ከኤባ ዝርያ ፊት ለፊት፣ እ አ አ ኦክቶበር 2022፡፡ ፎቶ ዘሪሁን ታደለ

አርሶ አደሩ በኤባ ማሳ ዉስጥ በምዕራብ አርሲ ዞን፣ አዳባ ወረዳ፣ ፉሩና ቀበሌ፤ እ አ አ ኦክቶበር 2022፤ ፎቶ ዘሪሁን ታደለ

በጤፍ ምርምር ካደረጉት ከፍተኛ አስተዋጽኦ በተጨማሪ የጉጉል ፍለጋ እንደሚያሳየኝ ዶ/ር ታደሰ ኤባ ከነ ዶ/ር አማረ ጌታሁን ጋር በመሆን በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የሚገኙ የእፅዋት ናሙናችን በማሰባሰብ ላይ ተሳትፈዋል፡፡ ይህም የዛሬ 45 አመት ገደማ መሆኑ ነዉ፡፡

በመቀጠልም እ አ አ ከ1968 እስከ 1971 ድረስ የመጀመሪያዉ የእፅዋት ጄኔቲክ ሀብት ማዕከል (PGRC/E) ወይም ያሁኑ የኢትዮጵያ ብዝሃ ሕይወት ኢንስቲትዩት (EBI) ዳይሬክቴር ሆነዉ ለሶስት ዓመታት እንዳገለገሉየመሥራያ ቤት ድረ ገጽ ያሳያል https://ebi.gov.et/ ፡፡ ምንም እንኳ ይኸዉ ምሥሪያ ቤት የአሁኑን ስም ከማግኘቱ በፊት በተለያየ ወቅት በተለያየ ስም (PGRC/E, EBIR, IBC, EBI) ቢጠራም እስካሁን ድረስ ባብዘኛዉ ሰዉ የሚታወቀዉ ‘ጂን ባንክ’ በሚለዉ ስም ነዉ፡፡

ከኢትዮጵያ ብዝሃ ሕይወት ኢንስቲትዩት (EBI) ድረ ገጽ ያገኘሁት መረጃ እንደሚያሳየዉ የዶ/ር ታደሰ ኤባ ፎቶ ይህን ይመስላል፡፡ https://ebi.gov.et/ accessed 20.12.2022፡፡ እንደሚመስለኝ ይህ ፎቶ ዶ/ር ታደሰ የመሥራይ ቤቱ የመጀመሪያዉ ዳይሬክተር የነበሩ ጊዜ የተነሱት ነዉ፡፡

ማጠቃለያ

ዶ/ር ታደሰ ኤባ የዛሬ 50 ዓመት አካባቢ በተለያዩ የጤፍ ዓይነቶች ላይ ባደረጉት ጥልቅ ምርምር ዝርያዎችን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ በመከፋፈል ድንቅ ሥራ ሰርተዋል፡፡ ይህንኑ ሥራቸዉን በመጽሐፍ አሳትመዉልናል፡፡ ነገር ግን መጽሐፋቸዉ በአሁኑ ጊዜ ለተጠቃሚዎች በቀላሉ ሊገኝ ባለመቻሉ የሚመለከታቸዉ አካላት ለሁሉም በሚዳረስበት መንገድ (open access) አሳትመዉ አቅርቦቱን እንዲያሳድጉ የራሴን ሀሳብ አቀርባለሁ፡፡ በስማቸዉ የሰየምነዉ የጤፍ ዝርያም ረዘም ላለ ጊዜ ከፍተኛ ተቀባይነት አግኝቶ እንደሚቆይም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ዶ/ር ታደሰ ኤባ የቀድሞዉን የእፅዋት ጄኔቲክ ሀብት ማዕከል (PGRC/E) ወይም የአሁኑን የኢትዮጵያ ብዝሃ ሕይወት ኢንስቲትዩት (EBI) የመጀመሪያው ዳይሬከር በመሆን መምራታቸዉም ልዩ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚሁ በሁለት ክፍሎች ያዘጋጀሁትን ስለ ዶ/ር ታደሰ ኤባ የሚያወሳዉን ጽሑፍ አጠናቅቃለሁ፡፡ እኝህ ታላቅ የጤፍ ምሁርም የዛሬ ስድስት ወር ገደማ ክዚህ አለም በሞት እንደተለዩን ሰምቻለሁ፡፡ ለዘመዶቻቸውና ባልደረቦቻቸዉ መጽናናትን እመኛለሁ፡፡

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 11፣ 2015 ዓ.ም. (December 20, 2022)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ ታዋቂዉ የጤፍ ታክሶኖሚስት፤ ታደሰ ኤባ፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ታዋቂዉ የጤፍ ተመራማሪና ታክሶኖሚስት፤ ታደሰ ኤባ፤ ክፍል 1

ዶ/ር ታደሰ ኤባን በይበልጥ የምናዉቃቸዉ በተለያዩ የጤፍ ዝርያዎች ላይ ጥልቅ ጥናት ካካሄዱ በኋላ ባበረከቱልን ሁለት መጽሐፍት ነዉ፡፡

እነርሱም

  1. እ አ አ በ1969 የታተመዉና ‘Tef (Eragrostis tef): the Cultivation, Usage and Some of the Known Diseases and Insect’. Part I. Experiment Station Bulletin 60. HSIU, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia እና
  2. በ1975 የታተመዉና ‘Tef (Eragrostis tef) cultivar: Morphology and Classification’. Part II. Experiment Station Bulletin 66. Addis Ababa University, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia የተባሉት ናቸዉ፡፡

የዛሬዉ ጽሑፌ የሚያተኩረዉ በሁለተኛዉ መጽሐፋቸዉ ላይ ነዉ፡፡ ይህ 73 ገጽ የያዘዉ መጽሐፋቸዉ በእንግሊዘኛ ቋንቋ የተጻፈ ሲሆን ከዚህ ዉስጥ 12 ገጾቹ በአማርኛ የተጻፉ ናቸዉ፡፡ በዚህ መጽሐፍቸዉ ዶ/ር ታደሰ በርካታ ቁም ነገሮች አበርክተውልናል፡፡

ለጤፍ ተመራማሪዎች በከፍተኛ ደረጃ የሚያገለግለዉ የሁለተኛዉ የዶ/ር ታደሰ ኤባ መጽሐፍ የፊት ሽፋን ይህንን ይመስላል፡፡  ምንጭ፤ Ebba T. 1975. Tef (Eragrostis tef) cultivar: Morphology and Classification. Part II. Experiment Station Bulletin 66. Addis Ababa University, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia

በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች የሚበቅሉ የጤፍ ዝርያዎችን በማሰባሰብና በጥልቀት በማጥናት እንዲሁም ዝርያዎቹ እርስ በርስ ያላቸዉን ቅርበትና ርቀት በሳይንሳዊ መንገድ በማጥናትና በመተንተን በመጽሐፋቸዉ በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ ውጤታቸዉንም በማስረጃ ከማስደገፋቸዉም በላይ እያንዳንዱ ዝሪያ ከዬትኛዉ የሀገራችን ክፍል እንደተገኘም ጭምር አሳይተዋል፡፡

በመጽሐፋቸዉ ውስጥ ባስቀመጡት መለኪያና የሥርዓት ምደባ (ታክሶኖሚ) ላይ የሚሰሩ ሳይንቲስቶች በሚጠቀሙበት ዘዴ ተመርኩዘዉ የዝርያዎችን ትንታኔ እንዳሳዩ አሳይተዋል፡፡ እነዚህ ለታክሶኖሚ ስራቸዉ የሚያገለግሉ ክራይቴሪዎችን ለማሳየት በራሳቸዉ በሳሏቸዉ ሶስት ወካይ የሆኑና ድንቅ የሆኑ ሥዕሎች ለማሳየት ሞክረዋል፡፡ ሥዕሎቹን ራሳቸዉ ለመሳላቸዉ በሶስቱም ላይ ታ. ኤ. (ታደሰ ኤባ) የሚል ተጽፎባቸዉ ይታያል፡፡ ይህም ድንቅ የመሳል ችሎታቸዉን ያሳየናል፡፡

እነዚህ የጤፍ ዝርያዎችን የሚወክሉ ሶሰት የዶ/ር ታደሰ ኤባ ሥዕሎችና ገላጻቸዉን ጭምር ከዚህ በታች ማየት ይቻላል፡፡

ምንጭ፤ Ebba T. 1975. Tef (Eragrostis tef) cultivar: Morphology and Classification. Part II. Experiment Station Bulletin 66. Addis Ababa University, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia

ምንጭ፤ Ebba T. 1975. Tef (Eragrostis tef) cultivar: Morphology and Classification. Part II. Experiment Station Bulletin 66. Addis Ababa University, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia

ምንጭ፤ Ebba T. 1975. Tef (Eragrostis tef) cultivar: Morphology and Classification. Part II. Experiment Station Bulletin 66. Addis Ababa University, College of Agriculture, Dire Dawa, Ethiopia

ከላይ በተጠቀሱት መለኪዎች በመርኮዝ ዶ/ታደሰ የጤፍ ዝሪያዎችን በ35 ዓይነቶች የከፈሉ ሲሆን እያንዳንዱን ዝሪያ ከሌላው የሚለይበትን ባህርይ በመተንተን አቅርበዋል፡፡ ውጤታቸዉንም በፎቶግራፍ ጭምር አስደግፈዋል፡፡

ይህ የዶ/ር ታደሰ ኤባ መጽሐፍ ከዛሬ 47 ዓመታት በፊት የታተመ በመሆኑና በአሁኑ ጊዜ በቀላሉ ለአንባቢያን ሊገኝ የማይችል በመሆኑ በመጽሀፉ ዉስጥ የተጠቀሱትን 35 ዝሪያዎች ማሳየቱ ጠቃሚ መስሎ ስለታየኝ ከዚህ በታች በአጭሩ ቀርበዋል፡፡

ምንም እንኳ ዶ/ር ታደሰ በርካታ መለኪያዎችን በመጠቀም የምደባ ሥራ (ታክሶኖሚ) የሰሩ ቢሆንም እኔ ከዚህ በታች የማሳየዉ የዝሪያዉን ስም፣ የፍሬዉን ሽፋን ቀለም እና ዝሪያዉ ከየትኛዉ የጤፍ አብቃይ አካባቢ እንደተገኘ ብቻ ነው፡፡

  1. Ada አዳ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ብርሃን፣ 2750 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  2. Addisie አዲሴ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  3. Adoensis አዶአንሲስ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ነቀምቴ፣ 2400 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  4. Alba አልባ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ አድዋ
  5. Balami ባለሚ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  6. Beten ብትን፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  7. Bunninye ቡንኝ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ነጆ፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  8. Burssa ቡርሳ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ሐረር፣ 1856 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  9. Curati ኩራቲ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ዳሞታ፣ 2400 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  10. Dabbi ዳቢ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ባህር ዳር፣ 1840 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  11. Denkeye ድንክዬ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ሐረር፣ 1856 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  12. Dschanger ጫንገር፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ መምሳክ
  13. Enatite እናቲት፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  14. Fesho ፌሾ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ወሊሶ፣ 2200 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  15. Gea-Lamie ጂአ ለሜ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ነጆ፣ 2750 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  16. Goferie ጎፈሬ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ጂማ፣ 1750 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  17. Gommadie ጎማዴ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ አጋሮ፣ 1870 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  18. Gorradie ጎራዴ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ አለማያ፣ 2100 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  19. Hamrawe Murri ሀምራዊ ሙሪ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት አመሬሳ፣ 1860 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  20. Hatalla ሀተላ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ሐረር፣ 1856 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  21. Janno ጃኖ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ዳሞታ፣ 2140-2480 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  22. Karadebi ከራዴቢ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ጊምቢ፣ 2100 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  23. Key Agachem ቀይ አጋቸም፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  24. Kaye Murri ቀይ ሙሪ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ሂዳቡ ገናሲ፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  25. Manya ማኛ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2100 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  26. Murri ሙሪ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ዳሞታ፣ 2750 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  27. Purpurea ፑርፑርያ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ አድዋ
  28. Rosea ሮሲ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ደብረ ዘይት፣ 2000 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  29. Rubicunda ሩቢኩንዳ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ አድዋ
  30. Shawa-Generra ሸዋ ጊሚራ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ሸዋ ገሚራ፣ ከፋ
  31. Trotteriana ትሮትሪያና፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ዳሞታ፣ 2480 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  32. Tullu Nasy ቱሉ ናሲ፤ የፍሬዉ ቀለም ነጭ፤ የተገኘበት ሥፍራ ነጆ፣ 2400 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  33. Variegata ቫሪጋታ፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ነጆ። 1950 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ
  34. Viridis ቪርዲስ የፍሬዉ ቀለም ነጭ
  35. Zuccagniana ዙካኚያና፤ የፍሬዉ ቀለም ቀይ፤ የተገኘበት ሥፍራ ዳሞታ፣ 2480 ሜ ከባህር ጠረፍ በላይ

በክፍል 2 ዶ/ር ታደሰ ኤባ በጤፍ ምርምር ካበረኩት ከፍተኛ አስተዋዖ በተጨማሪ በሌላ መስክ ያበረከቱትን ለማካተት እሞክራለሁ፡፡ እንዲሁም በአሁኑ ጊዜ በጤፍ ማሻሻያ ላይ ያለን ተመራማሪዎች የኚህን አንጋፋ ሣይንቲስት አስተዋጽኦ ለማስታውስ ያደረግነዉን እዘግባለሁ፡፡

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 11፣ 2015 ዓ.ም. (December 20, 2022)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ ከጠፋሁበት ተመልሻለሁ!


በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ከጠፋሁበት ተመልሻለሁ!!

የጠፋሁት ከምጽፈዉ ብሎጌ እንጂ ከመኖሪያ ሥፍራዬ ወይም ከሥራ ገበታዬ አይደለም፡፡ የመጨረሻ ጽሑፌን የጻፍኩት መጋቢት 15 ቀን 2012 ዓ.ም. (March 24, 2020) የኮሮና በሽታ በግብርናችን ላይ የሚያደርሰዉን አሉታዊ ጎን በሚመለከት ነበር፡፡ ይኸን የመጨረሻ ጽሑፌን የጻፍኩት ከ33 ወራት በፊት ማለትም የዛሬ 1000 ቀናት መሆኑ ነዉ፡፡  ለዚህ ረጅም ጊዜ መጥፋቴ ለኔም በጣም ይገርመኛል፡፡

ለመጥፋቴ አንዱ ምክንያት ይኸዉ ከኮሮና ጋር የተገናኘ የእንቅስቃሴ ገደብ ሊሆን ይችላል፡፡ ኮሮና በግብርናችን ላይ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በኑሮአችን ማለትም በጉዞአችን፣ በትምህርታችን፣ በሥራችን፣ በኢኮኖሚያችን ወ ዘ ተ በአለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ የሆነ እክል አድርሶብናል፡፡  የኮሮና ሁኔታዎች ሲሻሻሉ ግን በሌላ አቅጣጫ ትኩረት አድርጌ ስለነበር ብሎጌን መጻፍ ረሳሁ፡፡ አሁን ግን አዲስ ተስፋ ሰንቄ ተመልሼ መጥቻለሁ፡፡

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 11፣ 2015 ዓ.ም. (December 20, 2022)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የኮሮና ቫይረስ በግብርናችን ላይ፣ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የኮሮና ቫይረስ በግብርናችን ላይ፣ ክፍል 2

የዛሬ ሶስት ወራት ገደማ ዉሃን በሚባለዉ የቻይና ከተማ አካባቢ የጀመረዉና በአጭር ጊዜ ዓለማችንን በማዳረስ ላይ ስለሚገኘዉና በኮሮና ቫየረስ ወይም በሣይንሣዊ ስሙ coronavirus disease-19 (ወይም ባጭሩ Covid-19) ምክንያት ስለሚከሰተዉ በሽታ በሰፊዉ ተዘግቧል። Corona የሚለዉ ቃል በዚህች አጭር ጊዜ ዉስጥ ከ2.6 ቢሊዮን በላይ በሆኑ መጣጥፎች ዉስጥ የተገለጸ ሲሆን በአማርኛም ኮሮና የሚለዉ ስም ከግማሽ ሚሊዮን በላይ በሆኑ ጽሑፎች ተገልጿል። ይህ የሚያሳየን ቫይረሱ በጤናችን ላይ በማድረስ ላይ ያለዉን ከፍተኛ ተጽእኖ ነዉ። ከዚሁ ቫይረስ ጋር በተያያዘ እስካሁን ድረስ 395,647 የሚሆን የዓለማችን ህዝብ የተጠቃ ሲሆን ከዚህ ዉስጥ 17,241 የሚሆኑት በሞት ሊቀጠፉ ችለዋል። የዓለም ጤና ድርጅት ያወጣዉ መረጃ እንደሚያሳየዉ ቫይረሱ እጅግ በከፍተኛ ፍጥነት በመስፋፋት ላይ ሲሆን እንደምሳሌነት የሚቀርበዉ የመጀመሪያዎቹ አንድ መቶ ሺህ ሰዎች የተጠቁት በ67 ቀናት ዉስጥ ሲሆን የሚቀጥሉት መቶ ሺህ ሰዎች ደግሞ በ11 ቀናት ብቻ ነበር። የሚገርመዉ ደግሞ የመጨረሻዎቹ አንድ መቶ ሺህ ሰዎች የተጠቁት በአራት ቀናት ብቻ መሆኑ ነዉ። ከአንድ ቀን በፊት የዓለም የጤና ድርጅትና ፊፋ በጋራ ባወጡት መግለጫ ህብረተሰቡ በዚህ አደገኛ ቫይረስ እንዳይጠቃ ማድረግ ስለሚኖርበት ጥንቃቄ ግንዛቤ ለመስጠት የተለያዩ አገራትን የሚወክሉ 28 ታዋቂ የእግር ኳስ ተጫዋቾች የተመረጡ ሲሆን እነርሱም በ13 ቋንቋዎች መልክታቸዉን ያደርሳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ብዙዎች እንደሚስማሙት በዚህ ክፉ ቫይረስ ምክንያት የዓለማችን ኢኮኖሚ በዚህ በያዝነው የአውሮፓዉያኑ 2020 እና በሚቀጥሉት ተከታታይ ዓመታት ከፍተኛ ጉዳት እንደሚደርስበትና አንዳንድ ሀገራትም ከሚደርስባቸዉ የኢኮኖሚ ድቀት ለማገገም ረዥም ጊዜ እንደሚያስፈልጋቸዉ ነዉ። በከፍተኛ ደረጃ የቫይረሱ ሰለባ በሆነችበት ቻይና በቅርቡ በአነስተኛና መካከለኛ ደረጃ ባሉ ድርጅቶች ላይ የተደረገዉ ጥናት እንደሚያሳየዉ 80 ፐርሰንት የሚሆኑ ድርጅቶች ወደ ቀድሞ ሥራቸዉ ሊመለሱ አለመቻላቸዉ ነዉ። እንዲሁም በጥናቱ ከተካተቱት ዉስጥ 20 ፐርሰንት የሚሆኑት ደግሞ የነበራቸዉ ጥሬ ገንዘብ ከአንድ ወር ያልዘለቀ ሲሆን እስከ ሶስት ወር የሚቆይ ጥሬ ገንዘብ የነበራቸዉ 64 ፐርሰንት የሚሆኑት ብቻ ነበሩ።

ዩ ኤስ ኤድ የሚባለዉ የአሜሪካ መንግሥት የበጎ አድራጊ ድርጅት ባልደረባ የሆኑ ኤክስፐርቶች ኮኖና ቫይረስ በዓለማችን የምግብ ዋስትና ላይ ሊያደርስ ይችላል ተብሎ የሚገመተዉን ክስተት በቅርቡ በጻፉት ብሎግ አስነብበዉናል። እንደ እነዚህ ጸሐፊያን አባባል እያንዳንዱ ሀገር የኮኖና ቫይረስ ሥርጭትን ለመግታት የሚያደርገዉ ዝግጁነትና የሚነድፈዉ ፖሊሲ በምግብ ዋስትና ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ይኖረዋል።

በዚሁ የኮሮና ቫይረስ ምክንያት የሚደርሰዉን ከፍተኛ የምግብ ዋስትና ችግር እንዴት መቀነስ እንደሚቻል ሌላ ጽሑፍ የጻፉት ደግሞ ሲሞንታ በልትራሚ የተባሉ የዓለም የምግብ ፕሮግራም ባልደረባ ናቸዉ። እንደ ጸሐፊዋ አባባል በዚሁ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ለከፍተኛ አደጋ የሚጋለጡ ሀገራት በተለይም በመልማት ላይ ያሉ ሀገራት በሽታዉን ለመከላከል የሚደረገዉ ዕርዳታ ብቻ ሳይሆን የምግብ ዋስትናቸዉንም ለማስጠበቅ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸዉ ያስገነዝባሉ። የዓለም የምግብ ፖሊሲ ምርምር ኢንስቲትቱዩት (IFPRI) በዚሁ የኮሮና ቫይረስና የምግብ ዋስትና ላይ ትኩረት ያደረጉ አምስት የብሎግ ጽሁፎችን በልዩ እትም አትሞ አዉጥቷል። እነዚህን ማንበቡ ጠቃሚ ይመስለኛል።

ወደፊት በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መጋቢት 15 ፣ 2012 ዓ.ም. (March 24, 2020)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የኮሮና ቫይረስ በግብርናችን ላይ

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የኮሮና ቫይረስ በግብርናችን ላይ

የዛሬ ሶስት ወራት ገደማ ዉሃን በሚባለዉ የቻይና ከተማ አካባቢ የጀመረዉና በአጭር ጊዜ ዓለማችንን በመላ በማዳረስ ላይ ስለሚገኘዉ በኮሮና ቫየረስ ወይም በሣይንሣዊ ስሙ coronavirus disease-19 (ወይም ባጭሩ Covid-19) ምክንያት ስተትከሰትዉ በሽታ ብዙ ተብሏል። ይህችን አጭር ብሎግ እስከምጽፍበት ድረስ 245,484 የሚሆን የዓለማችን ህዝብ በበሽታዉ የተያዘ ሲሆን ከዚህ ዉስጥ 10,031 የሚሆኑት በሞት እንደተለዩን ከሚወጣዉ ሪፖርት ማወቅ ይቻላል። ይህም የበሽታዉን የመግደል አቅም ወደ 4% ያደርሰዋል ማለት ነዉ። ከአጠቃላይ ሟቾች ዉስጥ 66.4% የሆኑት ከቻይናና ከኢጣሊያን ዉስጥ ናቸዉ። ነገር ግን በበጎ ጎኑ መታየት የሚገባዉ በበሽታዉ ከተያያዙት ህመምትኞች መካከል 86,035 የሚሆኑት ከህመሙ ሊፈወሱ መቻላቸዉ ሲሆን ሌሎችም በማገገም ላይ እንደሚገኙ ነዉ። ሌላዉ ተስፋ የሚሰጠው ነገር ከሶስት ወራት ከፍተኛ ዉጊያ በኋላ ቻይና በዚህ በሽታ ላይ ድል እየተቀዳጀች እንደሆነ ነዉ። ለዚህም ማሳያ የሚሆነዉ ለመጀመሪያ ጊዜ ላለፉት ሁለት ተከታታይ ቀናት በበሽታዉ በአገሯ ውስጥ አዲስ የተጠቃ ሰዉ አለመመዝገቡ ነዉ። የዚህን ክፉ በሽታ መስፋፋት ለመግታት ህብረተሰቡ ማድረግ ስላለበት ጥንቃቄ እያንዳንዱ ሀገር የራሱን ነባራዊ ሁኔታ ባገናዘበ መልክ መመሪያ ያስተላለፈ ከመሆኑም በተጨማሪ ለተግባራዊነቱም ቁጥጥር በማድረግ ላይ ይገኛል።

የዛሬዉ ጽሁፌ የሚያተኩረዉ ይህ በሽታ በኢኮኖሚያችን በተለይም በግብርናችን ላይ ያደርሳል ተብሎ የሚገመተውን ጠባሳ ለማሳየትና ይህንንም ጠንክረን ማለፍ እንድንችል የራሴን ምክር ለመለገስ ነዉ።

የዛሬ አምስት ዓመታት ገደማ በምዕራብ የአፍሪካ ሀገራት በተከሰተዉ የኢቦላ በሽታ ምክንያት የምግብ ወይም የእህል ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቶ ነበር። ለዚህ ዋናዉ ምክንያት በኢቦላ በሽታ አምራቹም ኃይል በመጠቃቱ እንደሆነ ይገመታል። ከሁሉ የሚያስደንቀዉ ግን ምንም እንኳ በኮኖና ቫይረስ ምክንያት የተከሰተዉ በሽታ በቻይና ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ለማሳደር ቢችልም የምግብ ዋጋ ላይ የጎላ ለውጥ እንዳላሳየ አንድ ዘገባ ይጠቁማል።

ከህንድ ሀገር የወጣ ጽሁፍ እንደሚያሳዉ ሀገሪቱ ከቻይና ጋር ባላት ከፍተኛ የምግብ ሸቀጦች ንግድ ምክንያት በቻይና በተከሰተዉ ወረርሽኝ ምክንያት በህንድ ሀገር የምግብ አቅርቦት ላይ አሉታዊ ጎን እንደሚኖረዉ ይተነብያል።

እንደ የተባበሩት መንግሥታት የንግድና ዕድገት ድርጅት ግምት በዚሁ የኮሮና ቫይረስ ምክንያት በዚህ በያዝነዉ የአዉሮፓዉያን ዓመት ብቻ የዓለማችን ኢኮኖሚ ቢያንስ በአንድ ትሪሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንደሚቀዛቀስ ነዉ።.

ምንም እንኳ በተለያየ የዓለማችን አካባቢዎች ያሉ ህዝቦች የግብርና እና የንጽህና መገልገያ እቃዎችን ከዚህ በፊት ባልታየ ሁኔታ በማግበስበስ ላይ የሚገኙ ቢሆንም በምዕራቡ ዓለም የጎላ የዋጋ ጭማሪ የታየ አይመስለም። ለምሳሌ እኔ የምኖርበት ሀገር በከፍተኛ የኮኖና ቫይረስ ጥቃት ምክንያት በሰዎች ዝውውር ላይ እገዳ ቢደረግም በምግብና ተዛማች ዕቃዎች ላይ የሚደረገዉ ዝውውር እገዳ ያልተጣለበት በመሆኑ የዋጋ ጭማሪ ሊታይ አልቻለም። ከዚህ ሌላ በከተማ ዉስጥ የሰዎች እንቅስቃሴ ላይ የተገደበ ቢሆንም በጎረቤቴ የሚገኙ ገበሬዎች መደበኛ የእርሻ ሥራቸዉን በማከናወን ላይ ይገኛሉ። ይህ የሚያሳየዉ ምንም እንኳ ጊዜው የከፋ ቢሆንም ህይወት መቀጠል ስላለበትና ህብረተሰቡም ለምግቡ በገበሬዉ ላይ የተመረኮዘ በመሆኑ የሀገሪቱ ገበሬዎች ኃላፊነታቸዉን በመወጣት ላይ ይገኛሉ።

በመጨረሻም የዓለም የጤና ድርጅት ዳይሬክቴር ጄኔራል የሆኑት ዶክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም ለአፍሪካ ሀገራት በአጽንኦት እንደተናገሩት በአህጉሩ የሚገኙ ሀገራት በኮሮና ቫይረስ ሊደርስ የሚችለዉን ጥቃት ለመከላከል ነቅቶ መጠበቅ ያስፈልጋል ባሉት እኔም የዛሬውን ጽሑፌን እደመድማለሁ።

ወደፊት በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መጋቢት 11፣ 2012 ዓ.ም. (March 20, 2020)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የስንዴ ልማት በመስኖ፣ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የስንዴ ልማት በመስኖ፣ ክፍል 2

በክፍል 1 ጽሑፌ ለማሳየት እንደሞከርኩት በሀገር ዉስጥ የስንዴ ምርትን በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ በታሰበዉና በአሁኑ ወቅት በመስኖ የሚለማዉን እርሻ ለመጎብኘት በነበረኝ ከፍተኛ ፍላጎት መሠረት የዚህ ፕሮጀክት አንዱ አካል ወደ ሆነው ወደ አፋር ክልል መቀመጫ ወደ ሆነችዉ ወደ ሠመራ ከዚያም የስንዴ ልማቱ ወደሚገኝበት ዱብቲና አካባቢዉ ተጓዝኩኝ። ምንም እንኳ በአሁኑ ጊዜ የምርምር አቅጣጫዬ በጤፍ ላይ ያተኮረ ቢሆንም የስንዴ እርሻን ለመጎብኘት ያነሳሳኝ በአሁኑ ወቅት በመካሄድ ላይ ያለዉን የስንዴ ልማትን በቅርበት ሆኜ ለማየት ነዉ። ሌላዉ ምክንያቴ የዩኒቨርስቲ ትምህርቴን በባችለር ዲግሪ ጨርሼ ወደ ሥራ ዓለም ስመደብ ለመጀመሪያ ጊዜ ምርምር ያካሄድኩት በስንዴ ላይ ስለነበር ነዉ። እኔ በዚያን ወቅት ተመድቤ የሠራሁበትና አሁን የጎበኘሁት አካባቢ በአየር ጸባይ ተቀራራቢነት አላቸዉ። ሁለቱም ሥፍራዎች የተራራቁ ቢሆኑም የአዋሽ ወንዝን በመጠቀም ነዉ የልማትም ሆነ የምርምር ሥራዎች የሚከናወንባቸዉ። በወረር ምርምር ማዕከል በስንዴ አግሮኖሚ ላይ የምርምር ሥራዬን በማከናዉንበት ወቅት የምርምር ፕሮግራሜ ትኩረት ያደረገዉ በአካባቢዉ ዋነኛ ሰብል የነበረዉን ጥጥን በማስከተል ስንዴ ሊዘራበት የሚችልበትን ሁኔታ ማጥናት ነበር። ከዚሁ ምርምሬ ጋር ተዛማችነት የነበረዉን ሥልጠናዉም በስንዴ አግሮኖሚ ላይ በዉጭ ሀገር ተከታትዬ ነበር። በዚህ የተነሣ ላለፉት ሶስት አሥርት ዓመታት በዓለም አቀፍም ሆነ በአገር አቀፍ ድረጃ የስንዴ ምርምርም ሆነ ልማት ያለበትን ሁኔታ በቅርበት ለመከታተል ፍላጎት ያደረብኝ።

ከዚህ በታች ባሉት ምስሎች እንደሚታየዉ በዱብቲና አካባቢዉ በመካሄድ ላይ ያለዉ የስንዴ የዘር ብዜት በደህና ሁኔታ እየተካሄደ እንደሆነ ነዉ። ከዚህ ሥፍራ የሚመረተው ስንዴም በሚቀጥለዉ ዓመት በሰፊዉ ለሚካሄደዉ የስንዴ እርሻ በዘርነት እንዲያገለግል የታሰበ ነዉ።

በአሁኑ ጊዜ በእሸትነት ደረጃ ላይ የሚገኘዉ የስንዴ ማሣ በዱብቲ አካባቢ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

በዱብቲ አካባቢ ለአጨዳ የደረሰ የስንዴ ማሣ ዉስጥ ሆኜ። ፎቶ ደስታ ገብሬ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

ከዘር ብዜቱ በተጨማሪ የዳቦና የማኮሮኒ ስንዴን ያካተተተ የዝሪያ መረጣ ምርምርም በመካሄድ ላይ ይገኛል። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

በአካባቢዉ ወጣቶች በመልማት ላይ የሚገኘዉን የስንዴ ማሣ ደስታ ገብሬ ሲያሳየኝ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

አነስተኛ ደረጃ የተከሰተዉን የስንዴ ዋግ በሽታ ለመግታት ርጭት ለማድረግ በዝግጅት ላይ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

አልፎ አልፎ የአፈር ጨዋማነት በስንዴ ተክል ላይ ጉዳት ለማድረስ ችሏል። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

በአካባቢዉ ያለዉን የእርሻና የግጦሽ መሬት በከፍተኛ ደረጃ በመዉረር ላይ የሚገኘዉ ፕሮሶፒስ (Prosopis juliflora) የተባለዉ ተክል። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

አደገኛዉ የፕሮሶፒስ ተክል የመኪና መንገድንም ተከትሎ በሰፊዉ ተንሰራፍቶ ይታያል። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፤ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

የስንዴዉን የልማት ፕሮጀክት እዉን ለማድረግ በርካታ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተሳትፎ በማድረግ ላይ ናቸዉ። እኔም የልማቱን ሥፍራና እንዲሁም ከ30 ዓመታት በፊት የማዉቃቸዉን አሁን ግን በከፍተኛ ሁኔታ የተለወጡትን የዱብቲና የአሳይታና ከተሞችን ያስጎበኘንና በፕሮጀክቱ ዉስጥ ጉልህ ሚና በመጫወት ላይ የሚገኘዉን የእርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት ባልደረባ የሆነዉን አቶ ደስታ ገብሬን ከልብ አመሰግናለሁ።

ወደፊት በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መጋቢት 7፣ 2012 ዓ.ም. (March 16, 2020)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የስንዴ ልማት በመስኖ፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የስንዴ ልማት በመስኖ፤ ክፍል 1

ቀደም ብሎ ‘የኢትዮጵያ የስንዴ አብዮት‘ በሚል ርዕስ በጻፍኩት ብሎጌ ለማሳየት እንደሞከርኩትሚያዚያ 12 ቀን 2011 የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ኡመር ሁሴን ከግብርና ምሁራን ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ በከፍተኛ ደረጃ የስንዴ ምርትን ለማሳደግ ዕቅድ እንደተነደፈ አሳዉቀዉ ነበር። ይህም ከዉጭ ወደ ሀገሪቱ የሚገባዉን የስንዴ መጠን በሂደት እንዲቀንስና ከአራት ዓመታት በኋላ ከነጭራሹ እንደሚገታ ገልጸዉ ነበር። በዚሁ መሠረት በዋናዉ የመኸር ወቅት ከሚመረተዉ ስንዴ በተጨማሪ የመስኖ ዉሃን በመጠቀም በዓመት ሁለት ጊዜ የሚመረትበት ሁኔታ ተነድፎ ነበር።

በአሁኑ ወቅት ከባለድርሻ አካላት ጋር በተደረገዉ የተቀናጀ ሥራ በበርካታ ሥፍራዎች ስንዴን በመስኖ የማልማቱ ሥራ እየተካሄደ ይገኛል። ከነዚህ ሥፍራዎች ዉስጥ የመካከለኛዉና የታችኛዉ አዋሽ አካባቢዎች ይገኙበታል። በነዚሁ ሥፍራዎች የስንዴ የዘር ብዜት እየተካሄደ የሚገኝ ሲሆን ዋና ዓላማዉም የተባዛዉ ዘር በሚቀጥለዉ ዓመት እየተስፋፋ ለሚካሄደዉ የስንዴ እርሻ በዘርነት እንዲያገለግል ታስቦ ነዉ።

እኔም ይህንኑ የልማት ሥራ በቦታዉ ተገኝቼ ለማየት በራሴ ፍላጎት ከአስር ቀናት በፊት ወደ ሰመራ ተጓዝኩኝ። ከዚያም አንዱ የልማት ማዕከል ወደ ሆነችዉ ወደ ዱብቲ አቀናሁ። ዱብቲንና አሳይታን የዛሬ 32 ዓመት ገደማ አውቃቸዋለሁ። በወቅቱ የመልካ ወረር ምርምር ማዕከል (በአሁኑ አጠራር፣ የወረር ምርምር ማዕከል) ተመራማሪ በመሆኔ በታችኛዉ አዋሽ የነበረዉን የጥጥ ልማት ለመገምገም የብሔራዊ የጥጥ ምርምር ኮሚቴ ከነበርነዉ ጋር እንጓዝ ነበር። እነዚህም ዶክተር በዳዳ ግርማ (አዳቃይ)፣ አቶ አባቡ ደምሴ (ኢንቶሞሎጂስት፣ በአሁኑ ጊዜ በህይወት የሌሉ)፣ ዶክተር ገረመዉ ተረፈ (ፓቶሎጂስት)፣ ዶክተር ጥላሁን ወርዶፋ (የመስኖ መሐንዲስ)፣ እኔም አግሮኖሚስት እና ሌሎችንም ያካተተ ቡድን ነበር። ምንም እንኳ በመካከለኛዉ አዋሽ የሚገኘዉ የወረር ምርምር ማዕከላችን የአየር ፀባይ አዳጋች የነበረ ቢሆንም ወደ 300 ኪ.ሜ. ከማዕከላችን ርቀዉ የሚገኙት የዱብቲ፣ የአሳይታና የሎጊያ የአየር ፀባይ ደግሞ ከዚህ የባሰ ነበር። በዚያ ፈታኝ የአየር ፀባይ ዉስጥ በተመደብንበት የጥጥ መደብ እያንዳንዱን የጥጥ ቅጠልና እምቡጥ አገላብጠን አይተን በተባይ ወይም በበሽታ የተጠቃዉን እንመዝግብ ነበር። ዉጤቱንም ቀጥሎ በምናደርገዉ ግምገማችን ላይ እንጠቀምበት ነበር። በአሁኑ ጊዜ የአፋር ክልል ዋና ከተማ ሆና የምታገለግለዉ የሠመራ ከተማ በዚያን ጊዜ አልተቆረቆረችም ነበር። ምንም እንኳ ሠመራ በቅርቡ የተመሠረተች ቢሆንም በአሁኑ ጊዜ የተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ያሉባት ከተማ ከመሆኗም በተጨማሪ የሠመራ ዩኒቨርሲቲና የሠመራ ሡልጣን አሊሚራህ ሀንፋሬ ኤርፖርት ይገኙባታል።

ምንም እንኳ በአሁኑ ጊዜ የምርምር ፕሮግራሜ በጤፍ ላይ ያተኮረ ቢሆንም ከመሃል ሀገር ራቅ ብሎ የሚገኘዉን የስንዴ እርሻ ለመጎብኘት ፍላጎት ያደረብኝ በሁለት ዋና ምክንያቶች ነዉ። የመጀመሪያዉ የአሁኑ የስንዴ ልማት ሀገሪቷ በያመቱ ወደ አገር ዉስጥ የምታስመጣውን የስንዴ መጠን የሚቀንስ በመሆኑ ይህንን ከፍተኛ የልማት ሥራ በቅርበት ሆኜ ለመመልከት ነዉ። ሁለተኛወ ምክንያቴ እኔም ከረጅም ጊዜ በፊት ከሀረማያ ዩኒቨርስቲ (በወቅቱ ኮሌጅ) በባችለር ዲግሪ ትምህርቴን እንደጨረስኩ የተመደብኩት በወረር ምርምር ማዕከል በቆላ ሰብሎች ላይ ምርምር ለማካሄድ ነበር። የስንዴ ምርምርም አንዱና ዋነኛዉ የምርምር ፕሮግራሜ ነበር። በዚሁ መሠረት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ስንዴንና የስንዴ ምርምርን በትኩረት ነዉ የምከታተለዉ። ምክንያቱም እንደ አግሮኖሚስት በበርካታ የስንዴ ምርምር ፕሮግራሞች ላይ ለመሳተፍ ችያለሁና ነዉ። በወቅቱ ዶክተር ጀማል መሐመድ የተባሉ ትምህርታቸዉን በጀርመን ሀገር በመከታተል ላይ የነበሩ ተመራማሪ ለዶክትሬት ትምህርታቸዉ ማሟያ የሚሆን የምርምር ሥራቸዉን በቆላ ስንዴ ላይ በማዕከላችን ይሠሩ ነበር። እኔም የምርምር ሥራዬን ሀ ብዬ ስጀምር በዚሁ የቆላ ስንዴ ፕሮግራም ላይ ተመድቤ የምርምር ሥራዬን ተያያዝኩኝ። የአዋሽ ወንዝን በመስኖ በመጠቀም በስንዴና በሌሎች ሰብሎች በርካታ የምርምር ሥራዎችን እንሠራ ነበር። አካባቢዉ የጥጥ እርሻ የተስፋፋበት በመሆኑ የምርምሩ ፕሮግራሙም ትኩረት የተሰጠዉ ለጥጥ ነበር። የስንዴ ምርምር ፕሮግራም ዋናዉ ትኩረት የነበረዉ በዓመት ሁለት ጊዜ ሰብል ለማምረት የሚቻልበትን ሁኔታ ለማጥናት ነበር። በዚሁ መሠረት ጥጥ በዋናዉ የሰብል ወቅት ተተክሎና ተለቅሞ ከማሣዉ ላይ ከተነሳ በኋላ የአየር ሙቀቱ በሚቀንስበት የጥቅምት ወር ስንዴን ለመዝራት ነበር። የስንዴ እርሻ ከዚያ በፊት በአካባቢዉ ያልተለመደ በመሆኑ ሙከራዎቻችን የዝሪያ መረጣ፣ የዘር መጠን፣ የዘር ወቅት፣ የማዳበሪያ መጠን፣ የዉሃ መጠንና ሌላም የምርምር ዓይነቶችን ያካተተ ነበር። በአነስተኛ የመሬት ስፋት ባላቸዉ የምርምር ማዕከላችን የምንሰራዉን ሥራ ስፋፊ በሆኑ በአካባቢዉ ባሉ የመንግሥት እርሻ ማሳዎች ላይም እንፈትሽ ነበር። እኔም በዚህ የስንዴ ምርምርና ልማት በነበረኝ ተሳትፎ ተመርጬ ሜክሲኮ ሀገር በሚገኘዉ ዓለም አቀፍ የበቆሎና የስንዴ ምርምር ማዕከል ለሰባት ወራት የተሰጠዉን ሥልጠና ለመከታትል ችያለዉ። ይህ በስንዴ አግርኖሚ ላይ የተዘጋጀዉ ሥልጠና የቲዎሪና የተግባር ትምህርት ያካተተ ከመሆኑም በላይ ከዚያ ቀደም ብሎ በዩኒቨርስቲ ቆይታዬ ካገኘሁት በላይ ከፍተኛ ዕዉቀት የገበየሁበት ነበር ማለት ይቻላል። ስለዚህ ነው ስንዴና የስንዴ ምርምር ከልቤ ውስጥ ናቸዉ የምለዉ።

የአሳይታ ከተማ ከፊል ገጽታ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፣ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.
የሎጊያ ከተማ ከፊል ገጽታ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፣ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.
የሠመራ ከተማ ከፊል ገጽታ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፣ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.
የሠመራ ከተማ ከፊል ገጽታ። ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፣ የካቲት 26፣ 2012 ዓ.ም.

የዚህ ጽሑፍ ክፍል ሁለት በሚቀጥለዉ ብሎጌ ይቀርባል። እስከዚያዉ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መጋቢት 6፣ 2012 ዓ.ም. (March 15, 2020)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የጤፉ መሐንዲስ፤ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሑፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የጤፉ መሐንዲስ፤ ዶክተር ታረቀ በርሄ፤ ክፍል 2

ማስገንዘቢያ፤ በተለይ ካልተገለጸ በስተቀር ሁሉም ጊዜ የተጻፈዉ እንደ አዉሮፓ አቆጣጠር ነዉ

በክፍል አንድ ስለ ዶክተር ታረቀ በርሄ አጠር ያለ የህይወት ታሪክና የሥራ ልምድ ለማሳየት ሞክሬአለሁ። በዛሬዉ ጽሑፌ ደግሞ ስለ እኚህ የጤፍ መሐንዲስ በሰፊዉ ስለሚታወቁበት አስደናቂ ግኝት በጥያቄና መልስ መልክ አቀርባለሁ።

ጥያቄ፤ ለበርካታ ዓመታት በተለያዩ ሀገራት ያደረጉትን ሥራ የዛሬ 10 ዓመት ካጠናቀቁ በኋላ ጡረታ ወጥተዉ ቁጭ አሉ?  ጡረታ ወጥቼ አላረፍኩም። በህይወት ዘመኔ ያካበትኩትን የሥራ ልምድ በመጠቀም የጤፍና የሩዝ ምርታማነት እንዲያድግ ኢትዮጵያ ዉስጥ ATA ተብሎ በተቋቋመው ተቋም የሩዝ ቫሊዉ ቼይን ፕሮግራም ዳይሬክቴር ሆኜ ሠርቻለሁ።

የጤፍ ማዳቀል ሲነሣ የእርስዎ ስም ይነሳል። እንዲሁም የእርስዎ ስም ሲነሳ የጤፍ ስም ይነሳል። እስቲ በጤፍ ተመራማሪዎች ዘንድ ከፍተኛ አድናቆት ሰለተሰጥዎት ክስተት ቢያወሱኝበጤፍ ማዳቀል ላይ ሁለት አበይት እክሎች ነበሩ። የመጀመሪያዉ የጤፍ አበባ በማለዳ ብቻ ለአጭር ጊዜ እንደሚከፈት አለመታወቁ ነዉ። ሁለተኛዉ ደግሞ የጤፍ አበባ እጅግ አነስተኛ በመሆኑ ያለ አጉሊ መነጽር በአይናችን ብቻ የማዳቀል ሥራ ማከናወን አለመቻላችን ነዉ። ስለዚህ የተሳካ የጤፍ ማዳቀል ሥራ ለማከናወን ሦስት ነገሮች እንዲሟሉ ያስፈልጋል። እነዚህም 1ኛ) ከ30-40 እጥፍ የሚጎላ ባይኖኩላር ማይክሮስኮፕ፣ 2ኛ) እጅግ የተሳለና ቀጭን ፎርሴፕስ እና 3ኛ) የማይንቀጠቀጥ እጅ ናቸዉ። እኔ በጤፍም ሆነ በሌሎች ሰብሎች ተመራማሪዎች ዘንድ በሰፊዉ ልታወቅበት የቻልኩት የጤፍ አበባ በማለዳ ብቻ ለአጭር ጊዜ የሚከፈትበትን ጊዜ ለመጀመሪያ ጊዜ ማግኘቴ ብቻ ሳይሆን ይህንኑ ግኝት በመጠቀምና እንዲሁም የራሴን የዓላማ ጽናት በማከል ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳካ የጤፍ ማዳቀል ሥራ ለማከናወን በመቻሌ ነዉ።

እንዴት ይህንን አስደናቂ ግኝት ሊያገኙ ቻሉ? ለዚህ ግኝት ልበቃ የቻልኩት በሥራዬ ላይ በነበረኝ ከፍተኛ ትዕግሥትና የዓላማ ጽናት ሲሆን ወደምፈልገዉ ግብ ለመድረስም በነበረኝ ቁርጠኝነት ነዉ።

የጤፍ አበባ ይህንን ይመስላል። ሁለቱ ረዘም ያሉ ጸጉራም አካላት የሴቴዉን ወገን የሚወክሉት ስቲግማ ሲሆኑ አጠር ብለዉ ያሉት ሦስት ጥንዶች አንተር ተብለዉ የሚጠሩትን የወንዴዉን ፖለን የያዙ ናቸዉ። በቀኝ በኩል የሚታየዉ ስኬል ባር 1 ሚ ሜ ይወክላል። ፎቶ፣ ሬጉላ ብሎሽ፣ በርን ዩኒቨርስቲ፣ ስዊዘርላንድ።

በምርምር ዉጤትዎ በመመርኮዝ በርካታ ጽሑፎች አሳትመዋል። ነገር ግን ስለ ጤፍ አበባ አከፋፈትና እንዲሁም ማዳቀል ያገኙትን አስደናቂ ግኝት የት ነዉ ያሳተሙት? በርካታ ጽሑፎች ባሳትምም ከዚህ ግኝቴ ጋር በሚገናኝ ያሳተምኳቸዉ ጽሑፎች ከዚህ በታች ያሉት ናቸዉ።

  1. Berhe T. 1975. Breakthrough in tef breeding technique. Food and Agriculture Organization (FAO) Information Bulletin, Cereal Improvement and Production for Near East Project 12(3):11-13, FAO, Rome.
  2. Berhe T. 1976. Brighter prospects for improving Eragrostis tef by breeding. In: Proceedings on Evaluation of Seed Protein alternatives by Mutation Breeding, 5-9 May 1975, Vienna, Austria. International Atomic Energy Agency (IAEA), Vienna. pp. 129-135.
  3. Berhe T. 1976. The door is open for green evolution in tef. pp. 208-213. In: Proceedings of the Sixth Annual Research Seminar, 12-14 Nov 1975, Addis Ababa, Ethiopia. Institute of Agricultural Research (IAR), Addis Ababa.
  4. Addis Zemen Gazetta. 1975. ዓመት-ምህረቱን እንጂ የህትመቱን ቀን አላስታዉስም።
እ.ኤ.አ. ከኦክቶበር 22 እስክ 24፣ 2019 በቢሾፍቱ በተካሄደዉ ዓለም-አቀም የጤፍ ወርክሾፕ ላይ ዶክተር ታረቀ በርሄ ንግግር ሲያደርጉ ይታያል። ፎቶ፣ ዘሪሁን ታደለ

በርካታ ሽልማቶችና እዉቅና እንዳገኙ ይታወቃል። እስቲ ከነዚህ ዉስጥ ዋነኞቹን ቢገልጹልኝ፤ በዉጭ ሀገራትም ሆነ በአገር ዉስጥ የተሸለምኳቸዉና የተሰጠኝ እዉቅና በአራት ከፍሎ ማየት ይቻላል።

  1. ከአለማያ የእርሻ ኮሌጅ የእጽዋት ሣይንስ ተመራቂዎች መካከል የላቀ ዉጤት በማግኘቴ (በ1969)
  2. የዕውቅና ሠርቲፊኬት
  3. በ50ኛዉ ዓመት የአለማያ ዩኒቨርስቲ ምሥረታ በዓል (በ2005)
  4. በመጀመሪያዉ የአፍሪካ ሩዝ ኮንግረስ (በ2006)
  5. ከሣሣካዋ አፍሪካ በታዋቂዉ የአረንጓዴ አብዮት መሐንዲስ ዶክተር ኖሮማን ቦርሎግ እና በቀድሞዉ የአሜሪካ ፕሬዘዳንት ካርተር የተፈረመ (በ2006)
  6. የወርቅ ሜዳሊያና ሠርቲፊኬት የተሸለምኩበት
  7. በ40ኛዉ ዓመት የደብረ ዘይት ምርምር ማዕከል ምሥረታ በዓል (በ2005)
  8. በ50ኛው ዓመት የኢትዮጵያ እርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት ምሥረታ በዓል (በ2008)
  9. የክብር ዶክትሬት ከመቀሌ ዩኒቨርስቲ (በ2014)

ከኢትዮጵያዊያን ተመራማሪዎች መካከል እንደ ጀግና (hero) የሚቆጥሯቸዉን ሶስት ምሁራን ቢጠቅሱልኝ፤ በጤፍ ምርምር ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ናቸዉ ብዬ የምገምታቸዉ ዶክተር መላክ ኃይል መንገሻ፣ ዶክተር ሠይፉ ከተማ እና ዶክተር ክበበው አሰፋ ናቸዉ።

ካልዎት ረዥም ልምድ በመነሣት ለወደፊቱ የጤፍ ምርምር የሚለግሱት ምክር ባጭሩ ቢያካፍሉኝ፤ በህይወት ዘመኔ የጤፍ ምርት በሄክታር ከ80 እስከ 100 ኩንታል እንደሚደርስ ምኞቴ ነዉ።

ስለዶክተር ታረቀ በርሄ በሁለት ክፍል የቀረበዉ ጽሑፌ በዚህ ያበቃል። ከርሳቸዉ ረዥም የሥራ ልምድ በተለይም በጤፍ ምርምር ካበረከቱት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ብዙ የምንማረዉ ይኖራል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።

በሌላ ጽሁፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ የካቲት 15፣ 2012 ዓ.ም. (February 23, 2020)