ግብርናችንን ለማዘመን፤ የጤፍን ፍሬ በእንክብል የማሳደግ አስፈላጊነት፤ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

የጤፍን ፍሬ በእንክብል የማሳደግ አስፈላጊነት፤ ክፍል 2

ባለፈዉ ጽሑፌ የዘር እንክብል (seed pelleting) ስለሚባለዉና የዘር ፍሬን በእንክብል መንገድ በመሥራት ምርታማነትን ማሳደግ እንደምንችል ለማሳየት ሞክሬአለሁ። በዛሬዉ ጽሑፌ ደግሞ ይህንን የዘር እንክብል በጤፍ ላይ በመጠቀም የተደረገዉን ጥረትና ውጤት በአጭሩ ለማስነበብ እሞክራለሁ።

ባለፈዉ ብሎጌ እንደገለጽኩት የዘር እንክብል በርካታ ጥቅሞች አሉት። ይህ የሰብል ማሻሻያ መንገድ ጤፍንም በዘመናዊ መንገድ ለማሻሻል ከፍተኛ እገዛ ያደርጋል። ምክንያቱም የጤፍ ዘር ወይም ፍሬ በጣም አነስተኛ በመሆኑ ገበሬዎች አስፈላጊ የሆነ የዘር መጠን ሊጠቀሙ አይችሉም። ለጤፍ የሚመከረዉ የዘር ብዛት 10 ኪሎ ግራም በሄክታር ሲሆን ገበሬዎቻችን ግን ይህ የዘር መጠን በቂ መስሎ ሰለማይታያቸዉ እስከ 30 ወይም 40 ኪሎ በሄክታር ድረስ ይጠቀማሉ። ይህ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የዘር መጠን የጤፍን ተክሎች ለከፍተኛ መተፋፈግ ከመዳረጉም በላይ ሰብሉን ለመጋሸብ ያጋልጣል። የጋሸበ ተክል ደግሞ የምርት ብዛቱም ሆነ ጥራቱ በከፍተኛ ደረጃ ይቀንሳል ማለት ነዉ። በጤፍ ላይ የሚከሰተዉን ይህን ከፍተኛ መጋሸብ ለመቀነስ ወይም ለመቋቋም የተለያዩ መንገዶች መጠቀም ይቻላል።

እነዚህ መንገዶችም በመጠኑ በጥናት ላይ ሲሆኑ ሌሎችም በጥቅም ላይ እየዋሉ ነዉ። ለምሳሌ የጤፍ ተክል ቁመት በማሳጠር ጠንከር ያለና መጋሸብን መቋቋም የሚችል ተክል ማግኘት ይቻላል። ሌላዉ መንገድ ደግሞ ቁመት የሚያሳጥሩ ሆርሞኖች (plant hormone) በተወሰነ መልክ በጤፍ ላይ የሚያጋጥመውን መጋሸብ መግታት ይቻላል። የዛሬዉ ጽሑፌ የሚያተኩረዉ የዘር እንክብልን በመጠቀም የጤፍ የዘር መጠንን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ብቻ ሳይሆን መጋሸብንም እንደሚቀንስ ነዉ።

በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ዉስጥ ያሉና ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ተመራማሪዎችና ተቋማት የጤፍ መጋሸብን ችግር ለመፍታት ከፈተኛ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ። አንዳንዶቹም አመርቂ ዉጤት እያገኙ ነዉ።

በዚሁ መሠረት በኢትዮጵያ እና ስዊዘርላንድ ባሉ ተመራማሪዎችና ተቋማት የተመሰረተዉ የጤፍ ማሻሻያ ፕሮጀክት የጤፍን ዘር ወይም ፍሬ በእንክብል መልክ ለማሳደግ ዕቅድ ነድፎ ወደ ሥራ ገብቷል። በዚሁ መሠረት የዘር እንክብልን ለመሥራት የሚያገለዉን በላቦራቶሪ ውስጥ የሚቀመጥ አነስተኛ ፔሌቴር (pelleter) ገዝቶ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲቱት ሥር በሚገኘዉ የደብረ ዘይት ግብርና ማዕከል እንዲመሠረት ተደረገ፤ ሥልጠናም አስፈላጊ ለሆኑ ተመራማሪዎችና ቴክኒሻኖች ተሰጥቷል።

በምስሉ የሚታየዉ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲቱት ሥር በሚገኘዉ የደብረ ዘይት ግብርና ማዕከል ውስጥ የሚገኘዉ የዘር እንክብልን ለመሥራት የሚጠቅመዉ ፔሌቴር (pelleter) ነዉ። ፎቶ፤ ዘሪሁን ታደለ

ምስሉ የሚያሳየዉ የዘር እንክብልን በጤፍ ላይ ለመሥራት የሚያስችላቸውን ሥልጠና በደብረ ዘይት ግብርና ማዕከል የሚገኙ ተመራማሪዎችና ቴክኒሻኖች ሲወስዱ ነዉ። ፎቶ፤ ዘሪሁን ታደለ

ከዚህ በታች በምስሉ እንደሚታየዉ የጤፍን ዘር በተለያየ መጠን በእንክብል መልክ በማሳደግ ተስማሚ የሆነዉን ለመምረጥ ሙከራ ተደርጓል። በክፍል 1 ጽሑፌ በገለጽኩት መሠረት የዘር እንክብል ለመሥራት ዘሩን ለማሳደግ ፓዉደር፣ ውሃ፣ ማጣበቂያ እና ዘር ያስፈልጋሉ። ዘሩን ለማሳደግ በዋናነት የሚረዳዉ ፓዉደር ከተለያዩ ነገሮች መጠቀም ይቻላል።

ከላይ በምስሉ የሚታየዉ በጤፍ ዘር ዙሪያ እንክብል በመሥራት የጤፍ ዘርን ለማሳደግ እንደምንችል ነዉ። በዚሁ መሠረት የ1000 ጤፍ ዘር በአማካይ ከሚመዝነዉ 0.38 ግራም እስከ 7.57 ግራም በማሳደግ በብቅለት እና እድገት ላይ ያለዉን ሁኔታ ለማጥናት ችለናል። በእንክብል ያልተሰራዉን ጤፍ እንደ አንድ ብንቆጥር (በምሥሉ በቀኝ በኩል የሚታየው ለማለት ነዉ) በግራ በኩል የሚታየዉ እስከ 20 እጥፍ ክብደት ይጨምራል ማለት ነዉ። ከላይ የሚታዩትን እንክብሎች ለመሥራት አገልሎት ላይ የዋሉት ፓውደሮች ለ5 እና15 እጥፍ የእንጨት ፍቅፋቂ ሲሆን ለ20 እጥፉ ደግሞ የሸክላ አፈር ነዉ። ፎቶ፤ ዘሪሁን ታደለ

የጤፍን ዘር በእንክብል መልክ መጠቀሙ ጤፍን በእጅና በብተና ከመዝራት ወጥታ በመዝሪያ ማሽን ወደ መዝራት ሊያሸጋግራት ይችላል። የጤፍ መዝራትን ለማቀላጠፍ የተለያዩ የመዝሪያ ማሽኖች ሊሰሩ የቻሉ ሲሆን አንዳንዶቹም በሙከራ ላይ ናቸዉ። የተለያዩ ተቋማትም ትኩረት አድርገዉ በመሥራት ላይ ሲሆኑ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰዉ በግብርና ምርምር ማዕከል ሥር የሚገኘዉ የመልካሳ ምርምር ማዕከል ነዉ። ማዕከሉ ከሰራቸዉ የጤፍ መዝሪያ መሣሪያዎች ውስጥ ከዚህ በታች የሚታየዉ በተለይም የኮትቻ አፈር ባለበት ቦታ ተመራጭ ነዉ። ምክንያቱም በጤፍ የዘር ወቅት ከመሬቱ እጅግ የመርጠብና የመጣበቅ ባህርይ የተነሳ ግዙፍ መሣሪያዎችን ወደ ማሣ ማስገባት አስቸጋሪ ስለሆነ ነዉ።

ምስሉ የሚያሳየዉ የጤፍ ዘርን በተለይም በኮትቻ ማሣ ላይ ለመዝራት በመልካሳ ምርምር ማዕከል የተሰራዉን መዝሪያ ነዉ። ፎቶ፤ ዘሪሁን ታደለ

በአጠቃላይ የጤፍ እንክብልን በመጠቀም የምንዘራዉን ዘር በተፈለገዉ ርቀት እንዲቀመጥ በማድረግ የሚፈለገዉን የተክል ብዛት ማግኘት እንችላለን። ያለበለዚያ የተክሉ ብዛት ከተወሰነ መጠን በላይ የበዛ ከሆነ ተክሎቹ እርስ በርሳቸው ለብርሃን፣ ለውሃ እና ለማዕድን ሽሚያ ያደርጋሉ። የሚደርሰዉ ጉዳት በዚህ ብቻ ሳያበቃ ተክሎቹ ስለሚጋሸቡ ወይም ስለሚወድቁ የምርት ጥራትና መጠን በከፍተኛ ደረጃ ሊቀንስ ይችላል። በእንክብል መልክ የተሰራዉን የጤፍ ዘርንም በዘመናዊ የጤፍ መዝሪያ በመጠቀም የጤፍ ሜካናዜሽን ለማሳደግ እንችላለን።

በዚሁ በሁለት ክፍሎች ያቀረብኩትን ‘የጤፍን ፍሬ በእንክብል የማሳደግ አስፈላጊነት’ የሚለዉን ጽሑፌን አበቃለሁ።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 21 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 29, 2023)

ግብርናችንንለማዘመን፤ የጤፍን ፍሬ በእንክብል የማሳደግ አስፈላጊነት፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

የጤፍን ፍሬ በእንክብል የማሳደግ አስፈላጊነት፤ ክፍል 1

በዚህ ጽሑፌ የዘር እንክብል ብዬ የተጠቀምኩት በእንግሊዘኛዉ ሲድ ፔሌቲንግ (seed pelleting) የሚባለዉን ይወክላል በሚል ነዉ። ምናልባት የተሻለ ቃል ከተገኘ ወደፊት አስተካክላለሁ።

ቃሉ የሚያመለክተዉ የፍሬዉን መጠን በማሳደግ ለተለያዩ ጠቃሚ የግብርና ተግባራት ሥራ ላይ የሚዉልወን እንክብልን ነዉ። በዚህ መሠረት የእንክብሉ መጠን በከፍተኛ ደረጃ ሊያድግ ይችላል ወይም የዘሩ ቅርጽ ለማሽን መዝሪይ እንዲያመች ተደርጎ ይሰራል ማለት ነዉ። ከዚህ በተጨማሪ የተባይ ወይም የበሽታ መከላከያ መድሃኒትም በእንክብሉ ላይ በመጨመር እንክብሉ ለተለያዩ ጥቅሞች ያገለግላል ማለት ነዉ።

እዚህ ላይ ማወቅ ያለብን ባንድ እንክብል ወስጥ የሚኖረዉ የዘር ብዛት አንድ ብቻ ሲሆን ባጋጣሚ የተለያዩ ግብአቶች አጠቃቀም የተነሣ ከአንድ በላይ ዘር በተወሰኑት እንክብሎች ውስጥ ሊኖሩ ይችላል።

እንክብሉን ለመሥራት የሚረዱ የተለያዩ መሳሪያዎች በገበያ ላይ አሉ። እነዚህም በላቦራቶሪ ውስጥ ማስቀመጥ የምንችላቸዉ አነስተኛ ማሽኖች አንስቶ በፋብሪካ ደረጃ አገልግሎት ላይ የሚዉሉ ግዙፍ ማሽኖችም ያካትታል።

በአጭሩ እንክብልን ለመሥራት የሚከተሉት ግብአቶች ያስፈልጋሉ።

  • ዘር
  • ፓውደር፤ የተፈጨ የእንጨት ፍቅፋቂ፣ ሸክላ አፈር፣ ወዘተ። እዚህ ላይ ጥንቃቄ ማድረግ የሚገባን ይህ የእንክብሉን መጠን ለማሳደግ የምንጠቀምበት ፓዉደር በዘሩ ላይ ስለሚጣበቅ በዘሩ ላይ አሉታዊ ጎን እንይኖነዉ ማወቅ ያስፈልጋል። ያለበለዚያ የዘር ብቅለት በከፍተኛ ደረጅ ይሰናከላል።
  • ግሉ ውይም ማጣበቂያ
  • ውሃ

እነዚህ ግባቶችንም በሚከተለዉ መንገድ የዘር እንክብል ለመሥራት ጥቅም ላይ ይዉላል።

እንክብሉ ሲሰራ ዘሩ በፓውደሩ ሙሉ በሙሉ ይሸፈናል። ቢሆንም ዘሩን እና ሌሎች ግባቶችን በቋሚነት በተተመነት ፍጥነት የሚያሽከረክረዉን የማሽኑ ክፍል እና የእንክብኑ ግባቶች ከሆኑት ደግሞ እንደ ፓዉደርና ማጣበቂያ ያሉት የአጨማመር ፍጥነት በእንክብሉ ጥራት ላይ ከፍተኛ ሚና ይጫወታሉ።

የዘር እንክብልን ለመሥራት ባብዘኛዉ ከዚህ በታች በተመለከተዉ ቅድመ ተከተል ነዉ።

  • በመጀመሪያ ለእንክብል ልንጠቀምበት ያሰብነዉን ዘር በማሽኑ ውስጥ ወደሚገኘዉ ሰሃን ወይም ትሬ ላይ መጨመር፣
  • በመቀጠልም ትሬዉን ያለማቋረጥ እንዲሽከረከር ማድረግ፣
  • ዘሮቹ እስኪረጥቡ ድረስ ማሽኑ ዉሃ እንዲረጭ ማደረግ፣
  • በመቀጠልም ማሽኑ እንክብሉን ለማሳደግ የሚረዳዉን ፓዉደር የረጠበዉ ዘር ላይ በስ ሱ እንዲረጭ ማድረግ፣ በዚህን ጊዜ ፓዉደሩ ዘሩ ላይ ይጣበቃል።
  • ቀጥሎ ፓውደሩን ዘሩ ላይ እንዲጣበቅ የሚረዳዉን ማጣበቂያ ውይም ግሉ በትንሹ የረጠበዉ ዘር ላይ እንዲረጭ ማድረግ፣
  • በመቀጠልም የተሰሩት እንክብሎች ከማሽኑ እንዲወጡና በተፈለገዉ የእንክብል መጠን ያለቱን ወደ ማድረቂያ ማሽን ማዛወር፣ የማድረቂያ ሁኔታ ከፍተኛ ጥንቃቄ ይፈልጋል። ምክንያቱም የሙቀት መጠንና የማድረቂያ ጊዜ ውይም ሰዓት መስተካከል ይኖርበታልና።

የዘር እንክብል ከሚያስገኝልን ጥቅሞች መካከል ዋናዎቹ የሚከተለት ናቸዉ።

  • የዘር ፍሬያቸዉ እጅግ አነስተኛ የሆኑና ክብደታቸዉም በጣም ዝቅተኛ የሆኑ ሰብሎችን በቀላሉ መዝራት ስለማይቻል በእንክብል መልክ በማሳደግና ከበድ እንዲሉ በማድረግ በቀላሉ በማሽን ወይም በእጅ ለመዝራት ይቻላል። ለምሳሌ የካሮትና የሽንኩርት ዘሮች እንዲሁም ጤፍ በዚህ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ።
  • የአንዳድ ዘሮች ውጫዊ ቅርጻቸዉ ክብ ባለመሆኑ በማሽን ለመዝራት አመቺ አይደሉም። ስለዚህ የእንክብልን ዘዴ በመጠቀም ዘሩ በማሽን ለመዝርት አመቺ ይሆናል። ለምሳሌ በአዉሮፓና አሜሪክ በሰፊዉ የሚበቅለዉና ስኳርን ለማምረት አገልግልት ላይ የዋለዉን ሹገር ቢት የሚባለዉ ሰብል የውጭዉ የዘሩ ቅርጽ ወጥነት የሌለዉ በመሆኑ በማሽን ለመዝራት አመቺ አይደለም። የእንክብልን ዜዴ በመጠቀም ክብ ቅርጽ ያለዉና በቀላሉ በማሽን ሊዘራ የሚችል ዘር በጥቅም ላይ ሊዉል ችሏል።

ከላይ ያሉት ምስሎች የሚያሳዩት የሹገር ቢት ዘር ሲሆኑ በግራ በኩል ያለዉ ዘሩ እንደታጨደ የሚመስለዉን ሲሆን በቀኝ በኩል ያለዉ ደግሞ በእንክብል መልክ የተሰራዉን ዘር ነዉ። ምንጭ፤ https://www.amazon.com/SeedRanch-Sugar-Beet-Seed-Lbs/dp/B01KLMKQVY

https://depositphotos.com/4322868/stock-photo-sugar-beet-seed.html

  • ባንዳንድ ሰብሎች ላይ እንክብልን በመጠቀም የብቅለት ጊዜን ማፋጠን ተችሏል።
  • ስብሎቻችን በተለያዩ በሽታዎችና ተባዮች እንዳይጠቁ እንክብሉን ከሰራን በኋላ በተሰራዉ እንክብል ላይ በስሱ ተባዩን ወይም በሽታዉን የሚከላከል መድሃኒት ማልበስ እንችላልን። ይህ በተሰራዉ እንክብል ላይ በተጨማሪነት የሚሰራዉ ተግባር የዘር ኮቲንግ (seed coating) ይባላል። በዚሁ መሠረት እንክብሉ ጥጨማሪ ጠቀሜታ ይኖረዋል ማለት ነዉ።

በአጠቃላይ የዘር እንክብል ዘዴን በመጠቀም የምንዘራዉን ዘር በተፈለገዉ ርቀት እንዲቀመጥ በማድረግ ለእያንዳንዱ ሰብል የሚያስፈልገዉን የተክል ብዛት እንዲጠበቅ ማድረግ እንችላለን። ያለበለዚያ የተክሉ ብዛት ከተወሰነ መጠን በላይ የበዛ ከሆነ ተክሎቹ እርስ በርሳቸው ለብርሃን፣ ለውሃ እና ለማዕድን ሽሚያ ያደርጋሉ። የሚደርሰዉ ጉዳት በዚህ ብቻ ሳያበቃ ተክሎቹ ሲለሚጋሸብቡ ወይም ስለሚወድቁ የምርት ጥራትና መጠን በከፍተኛ ደረጃ ሊቀንስ ይችላል።

በክፍል 2 ጽሑፌ የጤፍ ፍሬ ወይም ዘርን በእንክብል መልክ በማሳደግ የተገኘዉን ውጤት አስነብባችኋለሁ። ወደፊትም ይህን መንገድ በሰፊዉ በመጠቀም የጤፍ ምርትን እንዴት ልናሳድግ እንደምንችል ለማሳየት እሞክራለሁ። እስከዛዉ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 19 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 27, 2023)

ግብርናችንንለማዘመን፤ በግብርናችን ላይ የተደቀኑትን እክሎች ለመቋቋም ያለን ዝግጁነት

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

በግብርናችን ላይ የተደቀኑትን እክሎች ለመቋቋም ያለን ዝግጁነት

ግብርናችን ለተለያዩ ሠዉ ሰራሽ እና የተፈጥሮ እክሎች ወይም ተድራጎቶች የተጋለጠ ነዉ። እነዚህም ከግብርና በሚገኙ የተለያዩ ምርቶቻችን ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ያሳድራሉ። በተፈጥሮ ብቻ የሚከሰቱ እነዚህ የምርት ማነቆዎችን ብቻ ብንመለከት በርካታዎችን መዘርዘር ይቻላል። እነዚህም በዋናነት ከአየር ንብረት እና አፈር ጋር የተገናኙ ናቸዉ።

ከአየር ንብረት ጋር የሚገናኙት የዝናብ እጥረት ወይም መብዛት፣ የአየር ሙቀት ከተፈለገዉ በላይ መብዛት ወይም ማነስ፣ የአየር እርጥበት ከሚፈለገዉ መጠን ውጭ መሆን እና ሌሎችንም የሚያካትት ሲሆን አፈርን በተመለከተ የአፈር ኮምጣጤን፣ የአፈር ጨዋማነት፣ የአፈር መሸርሸርን፣ የአፈር ለምነትና ሌሎችንም ይጨምራል። በአየር ንብረት ለዉጥ እየተከሰቱ የመጡ እነዚህ የምርት ማነቆዎች ማየቱም እየተለመደ መጥቷል።  ከዚህ በተጨማሪ እንደ በሽታና ተባይ ያሉትም ሰብሎቻችንን ክፉኛ ይፈታተኑታል። አንዳንዶቹም ሰብሎቻችንን ከነጭራሹ የማዉደም አቅም አላቸዉ።

ምስሉ የሚያሳየዉ በጨው የተጎዳ መሬት ሲሆን የጨዉ መጠኑ ከፍተኛ በመሆኑ ለምግብነት ወይም ለሌላ አገልግሎት የሚዉሉ ተክሎችን ማብቀል አስቸጋሪ ነው። እኔም ቀደም ብዬ በሰራሁበት የመካከለኛዉ አዋሽ ባንዳነድ ሥፍራዎች በጨዉ የተጠቃ መሬት ማየት የተለመደ ነበር። ምንጭ፤ https://www.biosaline.org/news/2018-07-17-6571

በአሁኑ ጽሑፌ የእነዚህ የምርት ማነቆዎችን ዓይነትና ብዛት ለመዘርዘር ሳይሆን ከነዚህ የምርት ማነቆች ዉስጥ አንዱ ወይም ሁለቱ በከፍተኛ ደረጃ ቢከሰቱ የበለጠ ጉዳት እንዳያደርሱ ራሳችንን አዘጋጅተን አፋጣኝ ምላሽ መስጠት እንዳለብን ላማስገንዘብ ነዉ። ባለን ልምድ እነዚህ የተፈጥሮ አደጋዎች ከጊዜ ወደጊዜ ይከሰታሉ። አንዳንዶቹም በቋሚነት አብረዉን አሉ።

ለዚህ አንዱ የመፍትሔፍ አካል ሊሆን የሚችለዉ ከዚህ በፊት በሌላ ብሎጌ የገለጽኩት የፈጣን ሰብል ማሻሻያ መንገድ ነዉ። ምክንያቱም የፈጣን የሰብል ማሻሻያ በአጭር ጊዜ ወስጥ የሚፈለገዉን ባህርይ የያዘ ዝርያ ሊያስገኝልይ ያቻላልና። በርግጥ ሌሎች ዘዴዎችም ይኖራሉ። ለሁሉም እነዚህ በቋሚነት ያሉና በደንገት የሚከሰቱ አደጋዎችን ለመግታት ተዘጋጅተን መጠበቅ ይኖርብናል ብዬ እገምታለሁ።

እዚህ ላይ ከሌሎች ሀገሮች ልምድ መውሰድ እንችላለን። ለምሣሌ እ አ አ በ2011 በጃፓን ሀገር በተከሰተዉ ከፍተኛ የመሬት መንቀጥቀጥ የተነሣ ወደ 20 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ የሩዝ መሬት ጨዋማ በሆነ የባህር ዉሃ ተጥለቀለቀ። መሬቱን ያጥለቀለቀዉ ውሃ ቦታውን ሲለቅ እርሻዉ ግን በጨዉ እንደተበከለ ቀረ። በሀገሪቱ የሚገኙ ሳይንስቶች ያላሰለሰ ጥረት በማድረግና ወደ ስድስት ሺህ የሚጠጉ በሙቴሽን ብሪዲንግ የተገኙ የሩዝ ዝርያዎችን በመምረጥና በመፈተሽ የአፈር ጨዋማነትን የሚቋቋም አንድ ዝርያ ለማግኘት ችለዋል። ይህ በአገሪቱ የተደቀነዉን ችግር ለመፍታት በአጭር ጊዜ የተደረገዉ ጥረትና አስደናቂ ዉጤት ለእኛም ትምህርት ሊሆነን ይችላል።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 15 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 23, 2023)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የኢንዱስትሪዉ አብዮትና የከፋዉ ረሃብ፤ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

የኢንዱስትሪዉ አብዮትና የከፋዉ ረሃብ፤ ክፍል 2

በክፍል 1 ጽሑፌ ስለ መጀመሪያዉ የኢንዱስትሪ አብዮት አመጣጥና የሰዎች ባንድ አካባቢ መስፈር ለማሳየት ሞክሬአለሁ። ለነዚህ ባንድ አካባቢ ለሰፈሩ የፋብሪካ ሠራተኞችና ቤተሰቦቻቸው በተመጣጣኝ ዋጋ በአማራጭነት የቀረበዉ ምግብ ድንች ነበር። ድንች የኢንዱስትሪ አብዮት በእንግሊዝ ሀገር ከመከሰቱ አንድ መቶ ዓመት በፊት ከአሜሪካ አህጉር ወደ አዉሮፓ አህጉር ለመጀመሪያ ጊዜ የመጣዉና በአጭር ጊዜ የተስፋፋ ሰብል ነበር። የድንች ምርት ከፍተኛ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን በዉስጡ ከፍተኛ ካርቦሃይድሬት ያለዉ በመሆኑ ምክንያት በፋብሪካ ውስጥ ለሚሰሩ ሠራተኞች የጉልበት ምንጫቸዉ ነበር።

ታዲያ ድንች በከፍተኛ ሁኔታ በጥቅም ላይ በዋለበት ጊዜና የኢንዱስትሪዉ አብዮትም እየተስፋፋ በነበረበት ወቅት አንድ አሰቃቂ ክስተት ተፈጠረ። ይህም በከፍተኛ ሁኔታ የተንሰራፋ ረሃብ ነበር። በተለይም በወቅቱ ከእንግሊዝ ጋር አንደ አንድ ሀገር በምትቆጠረዉ አይርላንድ ዉስጥ የተከሰተ ነዉ። ይህ ክፉ ረሃብ የተከሰተዉ እ አ አ ከ1845 እስከ 1852 ባሉት ሰባት ዓመታት ነበር። ረሃቡም ትልቁ ረሃብ ወይም የአይርላንድ የድንች ረሃብ ተብሎ ይታወቃል። በዚሁ ረሃብ የተነሣ ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ ሰዉ ሲሞት ወደ 2 ሚሊዮን የሚጠጋ ደግሞ ለመሰደድ ችሏል። በተለይም የአይርላንዶች በከፍተኛ ደረጃ ወደ አሜሪካ ለመሰደድ መንስኤዉ የዚህ የከፋ ረሃብ ነበር። በዚሁ ከፍተኛ የሞትና ስደት ምክንያት የአይርላንድ ህዝቧ ብዛት በ25% ሊቀንስ ችሏል።

በአይርላንድ የተከሰተዉ የታላቁ ረሃብ በዚህና በሌሎች ምስሎች ይመሰላል። ምንጭ፤ https://www.science-photo.de/bilder/12902897-The-Irish-Famine-1845-1849-1900

ለዚህ ረሃብ መከሰት ዋናዉ መንስዔ በወቅቱ በከፍተኛ ደረጃ ለምግብነት የሚያገለግለዉ የድንች ምርት በበሽታ ምክንያት ከምርት ውጭ መሆን ነበር። ከዚህ በታች እንደሚታየዉ በሽታዉ የድንችን ተክል ብቻ ሳይሆን የሚበላዉን የድንች አካልም በከፍተኛ ደረጃ ያጠቃል። ይህ በሽታም የድንች ሌት ብላይት (Potato late blight) ተብሎ ተሰይሟል። ይህ የድንች በሽታም የዕጽዋት በሽታ ምርምር (Plant Pathology) እንዲጀመርና እንዲስፋፋ ምክንያት ሆኗል።

ከላይ በምስሉ እንደሚታየዉ የድንች በሽታ በተክሉም ሆነ በድንቹ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል። ምንጭ፤ ተክል: https://www.vegetables.cornell.edu/crops/potatoes/late-blight/  ድንች፤ https://farmtario.com/news/ontaglate-blight-in-potatoes-detected-in-norfolk-county/

ይህ ሚሊዮኖችን ለአደጋ ያጋለጠዉ የድንች በሽታ መንስኤዉ ፋይቶፍትራ ኢንፌስታንስ (Phytophtra infestans) የተባለ ረቂቅ ህዋስ እንደሆነ የታወቀዉ ቆይት ብሎ ነዉ።

ከታች በምሥሉ እንደሚታየዉ የዚህ ረቂቅ ህዋስ መነሻዉ አሜሪካ ሲሆን በሽታዉ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ አዉሮፓ ተሻግሮ እና የድንችን እርሻ በማውድም እ አ አ ከ1845 ጀምሮ የተከሰተዉን ረሃብ እንዲከሰት ምክንያት ሆኗል።

ምስሉ የሚያሳየዉ የድንች ምርትን በከፍተኛ ደረጃ የጎዳዉ ፋይቶፍትራ ኢንፌስታንስ (Phytophtra infestans) የተባለው ረቂቅ ህዋስ ሥርጭትን ነዉ። መነሻዉ አሜሪካ ሲሆን ከ1845 ጀምሮ ለሰባት ዓመታት በአይርላንድ ለተከሰተዉ ከፍተኛ ረሃብ መነሻ የሆነዉ በቀዩ መስመር የሚታየዉ ነዉ። ምንጭ፤ https://elifesciences.org/articles/00731

ማጠቃለያ

ምንም እንኳ እጅግ በርካታ ምርምር በተለያዩ ሀገራት እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ቢደረግም እና አመርቂ ዉጤት ቢገኝም ፋይቶፍትራ ኢንፌስታንስን በቀላሉ በቁጥጥር ሥር ማድረግ አልተቻለም። እስከ ዛሬም ድረስ ቀላል ያልሆነ ጉዳት በድንቻችን ላይ እያደረሰ ይገኛል። ምክንያቱም ጥቃት በጀመረ ጥቂት ጊዜያት ውስጥ የድንችን ተክል ሊያወድም ይችላል። የጥቃት አድማሱንም በማስፋት በበርካታ ሀገራት ኢትዮጵያን ጨምሮ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል። የተቀናጀ የበሽታ ቅጥጥርን ማድርግ እንደሚያስፈልግ ይመከራል። ይህም የተሻሻሉ የድንች ዝርያዎች፣ ኬሚካሎች እና በተለይም የሰብል ፈረቃ መጠቀምን ያካትታል።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 15 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 23, 2023)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የኢንዱስትሪዉ አብዮትና የከፋዉ ረሃብ፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

የኢንዱስትሪዉ አብዮትና የከፋዉ ረሃብ፤ ክፍል 1

በተለምዶ የኢንዱስትሪ አብዮት ተብሎ የሚታወቀዉ የሚያመለክተዉ የሰዉ ልጅ ለመጀመሪያ ጊዜ በእጅ ከሚሰሩ የማምረቻ መንገዶች ወደ ማሽኖች እና ተጓዳች ዕቃዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ያሳደገበት ጊዜን ነዉ። በዚሁ ወቅት የብረት ማቅለጥና ጥቅም ላይ ማዋል፣ በእንፋሎት እና በዉሃ ኃይል የሚሰሩ መሣሪያዎች ሥራ ላይ ማዋል፣ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች መስፋፋት እና ለተለያዩ ተግባራት የሚዉሉ ኬሚካሎች የተገኙት ወቅት ነዉ።

የመጀመሪያዉ የኢንዱስትሪ አብዮት የተከናወነዉ እ አ አ ከ1760 እስከ 1840 ባለዉ ጊዜ ነዉ። ይህ የመጀመሪያዉ የኢንዱስትሪ አብዮት የተጀመረውና የተስፋፋዉ በእንግሊዝ ሀገር ሲሆን በመቀጠልም በቤልጂይም እና በፈረንሳይ እንደተስፋፋ ታሪክ ያስረዳናል።  ምንም እንኳ ጀርመን በወቅቱ ለነበረዉ የእንዱስትሪ አብዮት ጠቃሚ የሆነ የድንጋይ ከሰልና የብረት ማዕድናት ቢኖራትም ወደ እንዱስትሪ አብዮት የገባችዉ ዘግይቶ ነዉ። በመቀጠልም የኢንዱስትሪዉ አብዮት ወደ አሜሪካና ጃፓን ተሸጋገረ።

ከኢንዱስትሪ አብዮት በፊት በነበረዉ ጊዜ አብዘኛዉ ሰዉ የሚተዳደረዉ በግብርና ነበር። ቢሆንም ከግብርና የሚገኘዉ ምርት አነስተኛ በመሆኑ የህዝቡ ኑሮ ከእጅ ወደ አፍ እንደሆነ ይገመታል። የኢንዱስትሪ አብዮት በግብርናም መስክ ከፍተኛ ለውጥ አምጥቷል። ምክንያቱም አንዳንድ ለእርሻ ተግባር የሚዉሉ ማሽነሪዎችም በጥቅም ላይ ሊዉሉ የቻሉበት ወቅት ነበርና። ለምሳሌ አነስተኛ የዘር መዝርያ ማሽን እና ማዳበሪያዎች ተፈልስፈዉ ነበር።

በአጠቃላይ በመጀመሪያዉ የኢንዱስትሪ አብዮት ከተከናወኑ ዉስጥ የሚከተሉ አበይት ፈጠራዎች ወይም ክንዉኖችይጠቀሳሉ።

በጨርቃ ጨርቅ መስክ፤ ከፍተኛ ፍጥነት ያላቸዉ የጥጥ ማዳመጫና ልብስ የሚሰሩ ፍብሪካዎች ተፈልስፈዋል።

የኃይል ምንጭን በሚመለከት፤ በድንጋይ ከሰልና የእንፋሎት ጉልበት የሚጠቀሙ ፋብሪካዎች፣ መርከቦችና ባቡሮች በጥቅም ላይ ሊዉሉ ችለዋል።

ብረትን ለተለያዩ ተግባራት ሥራ ላይ ማዋል፤ የትላልቅ የብረት ማቅለጫ ፋብሪካዎች መፈልሰፍና የባቡር ሀዲድ፣ መርከብ ወ ዘ ተ ለመገንባት ሥራ ላይ መዋል።

አነስተኛ ማሽነሪዎችን በሚመለከት፤ ለተለያየ አገልግሉት የሚዉሉ በርካታ ማሽነሪዎች ሊፈለሰፉና ወደ ሥራ ሊገቡ ችለዋል።

ኬሚካልን በተመለከተ፤ ለተለያዩ ተግባራት የሚያገለግሉ ኬሚካሎች የተገኙ ሲሆን እነርሱም በጨርቃ ጨርቅ፣ ማዳበሪያ፣ ሲሚንቶ ወዘተ መስክ በሰፊዉ ሥራ ላይ የዋሉበት ጊዜ ነበር።

ከዚህ በተጨማሪ ሌሎች በርካታ ፈጠራዎች በተለያዩ መስኮች በጥቅም ላይ ሊዉሉ ችለዋል።

ስለዚህ የኢንዱስትሪ አብዮት በሰዉ ልጆች ታሪክ አንድ ከፍተኛ እመርታ ወይም ለዉጥ የታየበት ጊዜ ነበር። ይህ በቴክኖሎጂና ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ለዉጥ ያመጣዉ ክስተት በማህበራዊና ባህላዊ ድርጊቶች ላይም የጎላ ለዉጥ ሊያመጣ ችሏል። ምክንያቱም ሠራተኞች በፋብሪካዎች ተቀጥረዉ መስራት የጀመሩበት ጊዜ በመሆኑ የኑሮ ሁኔታቸዉ ከአሰሪያቸዉ በሚከፈላቸዉ አነስተኛ ደመወዝ እንዲመሰረት የተደረበት ነበር። ተገቢ የሆነ የአሰሪና ሰራተኛ ህጎች ስላልነበሩ አሰሪዎች ሰራተኞቻቸዉን በፈለጉት ጊዜ ሊያባርሯቸዉ ይችሉ ስለነበር ከሥራ ውጭ የሆኑ ሠራተኞች እና ቤተሰቦቻቸዉ ለከፋ ችግር ይዳረጉ ነበር።

የእንዱስትሪ አብዮትን ከሚወክሉ ምስሎች አንዱ። ምንጭ፤ https://baristaguild.coffee/blog/leaves-beans-of-history-the-industrial-revolution

ከላይ የተጠቀሱት የተለያዩ ኢንዱስትሪዎች እየተስፋፉ በመምጣታቸዉ እና የሰዎች በሚሰሩበት ፋብሪካዎች አቅራቢያ መስፈር ሰለነበረባቸዉ የከተሞች መመስረትና መስፋፋት ሊመጣ ችሏል። በፋብሪካዎቹ ወስጥ ለሚሰሩ ሰራተኞችና ቤተሰቦቻቸውም ረከስ ያለና በቂ ምግብ ያስፈልጋቸዉ ነበር። ለዚህ እንደ መፍትሔ የተቆጠረዉ  የኢንዱስትሪ አብዮት በእንግሊዝ ሀገር ከመከሰቱ አንድ መቶ ዓምት በፊት ከአሚሪካ አህጉር ወደ አዉሮፓ አህጉር ለመጀመሪያ ጊዜ የመጣዉና ምርት ውስጥ የገባዉ አንድ አስደናቂ ሰብል ነበር። እሱም ድንች ነበር። ድንች በአጭር ጊዜ ዉስጥ ከፍተኛ ምርት የሚሰጥ በሆኑ እጅግ ተወዳጅነትን አትርፎ አትርፎ ነበር።

በክፍል 2 ጽሑፌ ከኢንዱስትሪዉ አብዮት ጋር በቀጥታ ባይያዝም በተዘዋዋሪ መንገድ አስተዋጽኦ ስለነበረዉ በአዉሮፓ በተለይም በአይርላንድ ስለተከሰተዉ የከፋ ረሃብ አስነብባችኋለሁ። ከድንች ጋር የሚገናኝበትንም በጽሑፌ አካትታለሁ።

እስከዛዉ መልካሙን እመኛለሁ። ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 14 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 22, 2023)

ግብርናችንንለማዘመን፤ ጤፋችንን የዘከሩ ቴምብሮች

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ፡፡

ጤፋችንን የዘከሩ ቴምብሮች

የፖስታ ቤት ቴምብሮች ለመጀመሪያ ጊዜ በሥራ ላይ የዋሉት በእንግሊዝ በ1840 እንደሆነና ኢትዮጵያም የመጀመሪያዉን ቴምብር መጠቀም የጀመረችዉ ከ54 ዓመታት በሃላ በ1894 እንደሆነ ታሪክ ይነግረናል፡፡ ቴምብሮች የተለያዩ ማራኪ ሥፍራዎችን፣ ታዋቂ ግለሰቦችን፣ ታሪካዊ ክስተቶችን እና ወደፊት የሚከናወኑ ታላላቅ ስብሰባዎችን ለማስተዋወቅ ጥቅም ላይ ይዉላሉ፡፡ ምንም እንኳ የቴምብሮች ዓይነት በየጊዜዉ የሚለዋወጡ ቢሆንም እኔ በግሌ ብዙ ጊዜ እመለከት የነበረዉ በኢትዮጵያ በሰሜን ተራሮችና እና በባሌ ተራሮች ብቻ የሚገኘዉን የቀይ ቀበሮ ምስል የያዘዉን ነበር፡፡

ምስሉ የሚያሳየዉ ብዙ ጊዜ በኢትዮጵያ ቴምብሮች ላይ እመለከት የነበረዉን ቀይ ቀበሮ ወይም ሰሜን ቀበሮን ነዉ፡፡

ነገር ግን ላለፉት በርካታ ዓመታት ኢትዮጵያ በርካታ የተለያዩ ዓይነት ቴምብሮችን ማሳተሟና ሥራ ላይ ማዋሏ እሙን ነዉ፡፡ በተለያዩ ሀገራት በርካታ ሰዎች ቴምበር ማሰባሰብ ላይ ፍላጎት ያላቸዉ ሲሆን በኢትዮጵያም በትርፍ ጊዜያቸዉ ቴምብር መሰብሰብ የሚያስደስታቸዉ ሰዎች አሉ፡፡

እኔም የዛሬ 33 ዓመት እ አ አ በ1990 የኢትዮጵያ ፖስታ ቤት ካሳተማቸዉ ቴምብሮች መካከል ጤፍን በተመለከተ የታተሙትን አምስት ቴምብሮች ይመለከታል፡፡ ጤፍን በተመለከተ የታተሙ ቴምብሮች ከዚያ በላይ ሊሆኑ ቢችሉም እኔ ቴምብሮቹን ያገኘሁት የዛሬ 30 ዓመት ገደማ የጤፍ ተመራማሪ በነበርኩ ጊዜ ነዉ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ እነዚህ አምስት ቴምብሮች ከኔ ጋር ናቸዉ፡፡ እኔም የጤፍ ምርምሬን ቀጥዬበታለሁ፡፡

ከዚህ በታች በምስሉ እንደሚታየው አምስቱ ቴምብሮች የተለያዩ ተግባራትን ይወክላሉ፡፡ ቴምብሮችም 5፣ 10፣ 20፣ 75 እና 85 ሳንቲም ዋጋ ነበራቸዉ፡፡

በኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት እ አ አ 1990 የታተሙ ጤፍን በተመለከተ የታተሙ አምስት ቴምብሮች

ማጠቃለያ

የፖስታ አገልግሎት ጤፍን በተመለከተ ሌሎች ቴምብሮችን አሳትሞ ከሆን መረጃ የለኝም፡፡ ቢሆንም እነዚህ አምስት ቴምብሮችም ቢሆኑ ጤፍን ለመላዉ ዓለም ለማስተዋወቅ ከፍትኛ ድርሻ አላቸዉ፡፡ እንደሚታወቀዉ ሁሉ ጤፋችን ብዙ የምንወድለት ባህርያት እንዳሉት ሁሉ አንዳንድ መሻሻል ያለባቸዉ ባህርያትም አሉት፡፡ መሻሻል ካለባቸዉ ዉስጥ በዋናነት የምጠቀሱት በሄክታር የሚገኘዉ ምርት አነስተኝነትና የምርጥ ዝርያዎች አብዘኛዉ ገበሬ ዘንድ አለመድረሳቸዉ ነዉ፡፡ ስለዚህ የጤፍን ምርት በሀገር አቀፍ ደረጃ ለማሳደግ በምርምር፣ በልማት እና ፖሊሲ የተሳተፍን ሁሉ በጋራ በመስራት የጤፍ ምርትን ማሳደግ ይኖርብናል፡፡ ምርቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ ካለበት 18 ኩንታል በሄክታር ከፍ እንደሚል ጥርጥር የለኝም፡፡ ምክንያቱም ምርጥ ዝርያንና አስፈላጊዉን ግባት የተጠቀሙ ገበሬዎች በሄክታር እስከ 35 ኩንታል ማምረት ችለዋልና፡፡

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 12 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 20, 2023)

ግብርናችንንለማዘመን፤ፈጣን የሰብል ማሻሻያ (Speed Breeding)፤ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ፡፡

ፈጣን የሰብል ማሻሻያ (Speed Breeding)፤ ክፍል 2

በክፍል 1 ጽሑፌ የሰብል ማሻሻያ በማድረግ አንድን ዝርያ ለማስለቀቅ ቢያንስ ከ10 እስከ 12 ዓመታት እንደሚፈጅ ጽፌ ነበር። በዛሬዉ ጽሑፌ የሰብል ማሻሻያ የሚወስደዉን ይህን ረጅም ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ለማሳጠር የሚረዳዉንና ፈጣን የሰብል ማሻሻያ (Speed Breeding) ተብሎ ስለተሰየመዉ አስደናቂ ፈጠራ አስነብባችኋለሁ።

ይህ የ Speed Breeding መንገድ ለመጀሪያ ጊዜ ሪፖርት የተደረገዉ የዛሬ አምስት ዓመት ከተለያዩ ሀገራት የተዉጣጡ 29 ተመራማሪዎች በጋራ ባሳተሙት ጽሑፍ ነዉ። ጽሑፉም የሚከተለዉ ነዉ፡፡ Ghosh et al. 2018. Seed breeding in growth chambers and glasshouses for crop breeding and model plant research. Nature Protocols 13: 2944–2963.

የዚህ ዉጤት ዋናዉ ሚስጥሩ ተክሎችን በየቀኑ ለረጅም ጊዜ ብርሃን በመስጠት አበባ ለማበብ እና ፍሬ ለማፍራት የሚወስድባቸዉን ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ማሳጠር ነዉ። የዚህ ፈር ቀዳጅ ሥራ ዉጤታማ የሆነዉ ለማበብ ረዘም ያለ ብርሃን በሚያስፈልጋቸዉ (ወይም long-day በሚባሉ) ሰብሎች ነዉ።  የዚህ ምርምር ሥራም long-day ከሆኑት ሰብሎች መካከል በስንዴ፣ ሲናር፣ ሽምብራ፣ አተር እና ጓያ ላይ አመርቂ ውጤት አሳይቷል።

Speed Breeding ዉጤታማ የሚሆነዉ ተክሎችን የተለያዩ የአየር ሁኔታችን መቆጣጠር የሚቻልበት ሥፍራ በማሳደግ ሲሆን በዋናነት ቁጥጥር የሚደረግባቸው የብርሃን ዓይነትና ጥራት፣ የብርሃን ርዝመት ወይም ርዝመት፣ የአየር ሙቀት እና የአየር እርጥበት ናቸዉ።

  • የብርሃን ዓይነትና ጥራትን በሚመለከት በተለምዶ PAR የሚባለውንና 400 እስከ 700 nm ሲሆን ሰማያዊ፣ ቀይ እና ፋር ቀይ የተባሉትን ያካትታል። የአምፑሎች ዓይነትም LEDs ወይም LED እና ሃሎጅን የሚባሉት ናቸዉ፡፡
  • የብርሃን ጊዜ ግሞ 22 ሰዓት ብርሃሁለት ሰዓት ብቻ ጭለማ ሆናል ማለት ነዉ።
  • የአየር ሙቀት ደግሞ በ22 ሰዓቱ የብርሃን ጊዜ 22 ድግሪ ሴንቲግሬድ ሆን በተቀረዉ የሁለት ሰዓት የጭለማ ጊዜ 17 ድግሪ ሴንቲግሬድ ነዉ።
  • የአየር እርጥበት ከ60 እስከ 70% መካከል ያለዉ ተስማሚ ነዉ።

ከላይ የተገለጹት መስፈርቶች በመጠቀም speed breeding በተወሰኑ ሰብሎች ላይ አመርቂ ውጤት ሊያስገኝ ችሏል። ከዚህ በታች በሥዕሉ እንደሚታየዉ 22 ሰዓት ብርሃን በመጠቀም በአንድ ዓመት ብቻ እስከ 6 ጊዜ የስንዴ፣ የገብስ ወይም የሽንብራ ዘር ማጨድ እንደሚቻል ሲሆን የሰብል አዳቃዮች በተለምዶ በሚጠቀሙበት መንገድ ግን በዓመት ሊገኝ የሚችለዉ ሶስት ጊዜ ብቻ ነዉ። ስለዚህ የ speed breeding መንገድ በክፍል አንድ ለገለጽኩት single seed descent (ነጠላ ዘር መዉረድ) መንገድ እጅግ አመቺ ነዉ፡፡

ከላይ በምሥሉ በግራ በኩል የሚታዩት 22 ሰዓት ብርሃን እና 2 ሰዓት ጭለማ በመጠቀም 6 የስንዴ፣ ገብስ ወይም ሽምብራ ሰብሎችን በአንድ ዓመት ማግኘት እንደሚቻል ነዉ፡፡ በቀኝ በኩል የሚታዩት ደግሞ በተለምዶ መንገድ ሊመረት የሚቻለዉ በዓመት  ሶስት ሰብሎች መሆኑን ነዉ፡፡ ምንጭ፤ በከፊል የተወሰደዉ ከ Ghosh et al. 2018. Seed breeding in growth chambers and glasshouses for crop breeding and model plant research. Nature Protocols 13: 2944–2963 ነዉ፡፡

የዚህ የፈጣን ሰብል ማሻሻያ መንገድ ለመጀመሪያ ጊዜ ሪፖርት ከተደረገበት እ አ አ 2018 ጀምሮ ከፍተኛ አድናቆትንና ተቀባይነትን ያተረፈ ሲሆን በተለያዩ ሰብሎች የሚሰሩ ተመራማሪዎች ስብሎቻቸዉን በአጭር ጊዜ ለማሻሻል እንዲያስችላቸዉ መጠነኛ ለውጥ በማድረግ ብቻ ውጤታማ ሊሆኑ ችለዋል፡፡ ለምሳሌ cowpea (ላም አተር) ላይ የተደረገዉ ሙከራ እንደሚያሳየዉ እስከ ስምንት ስብሎችን በአንድ ዓመት ሊያገኙ ችለዋል፡፡ ምንጭ፣ Edet and Ishil. 2020. Plant Methods 18:106.

ምንም እንኳ የመጀመሪያ ሥራዎች እንደሚያሳዩት ይህ ፈጣን የሰብል ማሻሻያ መንገድ ዉጤታማ የሆነዉ ረዘም ያለ የብርሃን ሰዓት ለሚያስፈልጋቸዉ ሰብሎች ብቻ ቢሆንም የተወሰኑ የብርሃን ሁኔታዎችን በማስተካከል አጠር ያለ የብርሃን ሰዓት ለሚያስፈልጋቸዉ ሰብሎችም ተግባራዊ ሊሆን ችሏል፡፡ በዚሁ መሠረት አጠር ያለ ብርሃን በሚያስፈልጋቸዉ እንደ ሩዝ፣ አኩሪ አተር እና አማራንተስ ላይ በመስራት እስከ አምስት ሰብሎችን በዓመት ለማጨድ ተችሏል፡፡ ምንጭ፤ Jähne et al. 2020. Theoretical and Applied Genetics 133: 2335-2342.

የዚህ የፈጣን የሰብል ማሻሻያ መንገድ ያለዉን ከፍተኛ ጥቅም በመረዳት የሰብል ተመራማሪዎች ብቻ ሳይሆኑ አንዳንድ ሀገራትም ማዕከል እስከማቋቋም ደርሰዋል፡፡ ለምሳሌ የህንድ መንግሥት በቅርቡ SpeedBreed የሚባል ማዕከል ቫራናሲ በሚባል ሥፍራ አስመርቋል፡፡

በህንድ ጠቅላይ ሚኒስቴር ተመርቆ ሥራዉን የጀመረዉ የፈጣን ሰብል ማሻሻያ ማዕከል ይህን ይመስላል፡፡ ማዕከሉ በዉስጡ ለፈጣን የሰብል ማሻሻያ የሚያገለግሉ በርካታ ክፍሎች አሉት፡፡ ምንጭ፤ https://www.irri.org/news-and-events/news/speedbreed-crop-breeding-center-built-speed

ማጠቃለያ

የፈጣን ሰብል ማሻሻያ ጥቅምን ከላይ ለመግለጽ ሞክሬአለሁ፡፡ ዋናዉ ጥቅሙ የሰብል ማሻሻያ ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ማጠሩ ነዉ፡፡ በተለይም ድንገተኛ እክሎች ለምሳሌ የሰብል በሽታ ቢከሰት ባፋጣኝ የማዳቀል እና የሰብል ማሻሻያ ፕሮግራሞችን እንድናከናዉን ይረዳናል፡፡ የዚህ የፈጣን ሰብል ማሻሻያ እንድንጠቀም የሚረዳን መሰረተ ልማት በሀገራችን እስካሁን ድረስ የለም፡፡ በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያስፈልግ ግን ጥርጥር የለኝም፡፡ ለምሳሌ ሰብሎቻችን በተደጋጋሚ ለበሽታዎች ይጠቃሉ፡፡ በተለይም ይህ ጥቃት በስንዴዎቻችን ላይ ይጠናል፡፡ ዋግ የሚባላዉ በሽታ መልኩንና ባህርዩን እየቀያየረ በቅርቡ ጸድቀዉ የወጡ ዝርያዎችንም ጭምር ሳይቀር በከፍተኛ ደረጃ ያጠቃል፡፡ ገበሬዎቻችንም ያለ ምርት ያስቀራቸዋል፡፡ ስለዚህ ቢያንስ አንድ የፈጣን ሰብል ማሻሻያ ማዕከል በብሔራዊ ደረጃ ማቁቋም አስፈላጊ አይደለም ትላላችሁ? በኔ አስተያየት አስፈላጊ ነዉ እላለሁ፡፡

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 11 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 19, 2023)

ግብርናችንንለማዘመን፤ፈጣን የሰብል ማሻሻያ (Speed Breeding)፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ፈጣን የሰብል ማሻሻያ (Speed Breeding)፤ ክፍል 1

የሰብል ተመራማሪዎች በዋናነት ትኩረት አድርገዉ የሚሰሩት የሰብል ምርት እንዲያድግ ነው፡፡ ይህም ሊሆን የሚችለዉ የምርት ማነቆ በሆኑት ላይ ትኩረት በማድረግ ነዉ፡፡ እነዚህ የምርት ማነቆዎች ወይም ተዳርጎቶች በርካታ ቢሆኑም በዋናነት ከሚጠቀሱት መካከል ድርቅ፣ የዉሃ ማቆር፣ ሙቀት፣ የሰብል መጋሸብ ወ ዘ ተ ን ያካትታሉ፡፡

እንደሚታወቀዉ ሁሉ ሰብሎቻችንን ለማሻሻል በርካታ መንገዶች አሉ፡፡ እስካሁን ድረስ በሰፊዉ በጥቅም ላይ የዋሉት የመረጣ (selection) እና የማዳቀል (hybridization) መንገዶች ናቸዉ፡፡ የማዳቀል ሥራ የሚሰራዉ የተለያዩ ባህርይ ያላቸዉን ሁለት ተክሎች በማጣመር ሁለቱም ጥሩ ባህርያት በሰብላችን ውስጥ እንዲካተት ለማድረግ ታስቦ ነዉ፡፡ ለምሳሌ  የዛሬ 15 አመት ገደማ በብሄራዊ የዝርያ አጽዳቂ ኮሚቴ ጸድቆ የወጣውና በአምራቾች ዘንድ ከፍተኛ አድናቆትን ያተረፈዉ ቁንጮ የተባለዉ የጤፍ ዝርያ የተገኘዉ የተለያዩ ባህርይ ያላቸዉን ሁለት የጤፍ ዝርያዎችን በማዳቀልና መጠነ ሰፊ መረጣ በማካሄድ ነዉ፡፡ ሁለቱ ለዚህ አገልግሎት የዋሉት የጤፍ ዝርያች ዱከም እና ማኛ ይባላሉ፡፡ የዱከም ዝርያ ከፍ ያለ ምርት የሚሰጥ ሲሆን የፍሬው መልክ ነጣ ያለ ቢሆንም በሸማቾች ዘንድ ያለዉ ተቀባይነት አነስተኛ ነዉ፡፡ በሌላ በኩል ማኛ የተባለዉ ዝርያ ስሙ እነደሚያመለክተዉ ፍሬዉ እጅግ በጣም ነጭ በመሆኑ በተጠቃሚዎች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት አለዉ፡፡ ነገር ግን የዚህ ዝርያ ምርት አነስተኝ ነዉ፡፡ ስለዚህ በሥራዉ የተሳፉት የጤፍ ተመራማሪዎች ዋና አላማ አድርገዉ የተነሱት ሁለቱን የጤፍ ዝርያዎች በማዳቀልና በተለያዩ ወካይ የጤፍ አብቃይ ሥፍራዎች በመፈተሽ ፍሬዉ እንደማኛ ነጭ፣ ምርቱ ደግሞ እንደ ዱከም ከፍ ያለ ለማግኘት ነበር፡፡ በርግጥ ሥራቸዉ መና አልቀረም፡፡ እንዳሰቡት ሆኖላቸዉ ሁለቱንም ጥሩ ባህርይ የያዘ ቆንጮ የሚባል ዝርያ እ አ አ በ2006 ለማስለቀቅ ችለዋል፡፡

ከማዳቀል አንስቶ ዝርያ እስከማጸደቅ ባለዉ ሂደትም የተለያዩ ተመራማሪዎች የተለያየ መንገድ ይጠቀማሉ፡፡ ለምሳሌ የብሄራዊ የጤፍ ምርምር ነጠላ ዘር መውረድ (single seed descent) የሚባለዉን መንገድ የጠቀማል፡፡ ከዚህ በታች በሥእሉ እንደሚታየዉ በዚህ መንገድ ከተጠቀምን ዝርያ ከማጸደቃችን በፊት እስከ ከ11 እስከ 12 የሰብል ወቅቶች ይፈጃል፡፡ በዚህ የሰብል ማሻሻያ መንገድ ለምንፈልገዉ ባህርይ የምንመርጠዉ ከሰባተኘዉ ወቅት በኋላ በመሆኑ እስከ ስድስተኛዉ ወቅት ድረስ አንድ ዘር ብቻ በመዉሰድ ወደ ሚቀጥለዉ ደረጃ እናስተላልፋለን ማለት ነዉ፡፡ በዚሁ መሰረት እስከ ስድስተኛዉ የሰብል ወቅት ወይም ደረጃ ያሉትን በመስታወት ቤት በማሳደግ ወይም በመስኖ በመጠቀም በአመት ሁለቴ ወይም ሶስቴ በማሳደግ የሚያስፈልገዉን ጊዜ ማሳጠር ይቻላል፡፡ ነገር ግን PVT and NVT የሚባሉት በአገሪቱ ወካይ በሆኑ ሥፍራዎች ስለሚፈተሹና አብዘኞቹ ሥፍራዎች የመስኖ አቅርቦት ስለሌላቸዉ በአመት አንድ ጊዜ ብቻ ለማሳደግ እንገደዳለን፡፡

ከላይ በምሳሌነት  እንደሚታየዉ ጠላ ዘር መውረድ (single seed descent) መንገድ ከማዳቀል ጀምሮ እስከ ዝርያ ማጽደቅ ያለዉ ሂደት እስከ 12 የሰብል ወቅት ወይም አመታት ይፈጃል፡፡ በመስኖ የመጠቀም እድሉ ካለ በአመት ሁለት የሰብል ወቅቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ አንድ ዝርያ ለማዉጣት የሚፈጀዉ ጊዜ በተወሰነ አመታት ሊያጥር ያችላል፡፡

ምንጭ፣ ተሻሽሎ የተወሰደ Chanyalew et al. 2019. Tef (Eragrostis tef) breeding. In: Al-Khayri JM, Jain SM, Johnson DV (Eds.), Advances in Plant Breeding strategies: cereals. Springer Nature AG.

ምንም እንኳ ይህ የ single seed descent ሆነ ሌሎች የሰብል ማሻሻያ መንገዶች ጠቃሚ ቢሆኑም እና በርካታ የተለያዩ ሰብሎችን ዝርያ ለማስለቀቅ ከፍተኛ አስተዋጸዖ ቢያደርጉም ረዘም ያለ ጊዜ የሚወስዱ በመሆኑ ለድንገተኛ (emergency) ወቅት ላይደርሱ ይችላሉ፡፡ በተለይም ሰብሎቻችንን በድግግሞሽ የሚያጠቁ በሽታዎችን ለመግታት ያዳግታል፡፡ ምክንያቱም የማሻሻያዉ ፕሮግራም በሂደት ላይ እያለ በሰብሎቻችን ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊደርስ ይችላል፡፡

በዚሁ መሰረት የሰብል ማሻሻያ የሚወስደዉን ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ለማሳጠር በተደረገዉ ጥረት በቅርቡ ጥሩ ዜና ደርሶናል፡፡ ይህም ፈጣን የሰብል ማሻሻያ (Speed Breeding) ተብሎ ተሰይሟል፡፡ እኔ በክፍል 2 ስለዚሁ ፈጣን የሰብል ማሻሻያ በሰፊዉ አስነብባለሁ፡፡

እስከዛዉ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥር 8 ቀን 2015 ዓ.ም. (January 16, 2023)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የቆላ ስንዴን በመስኖ ያስተዋወቁን ፤ ዶ/ር ጀማል መሐመድ፤ ክፍል 3

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የቆላ ስንዴን በመስኖ ያስተዋወቁን ፤ ዶ/ር ጀማል መሐመድ፤ ክፍል 3

በዛሬዉ ጽሑፌ ከዶ/ር ጀማል መሐመድ ጋር ባለፉት ጥቂት ዓመታት በጋራ ልንሰራ ስላቀድነዉ የምርምር ፕሮግራምና ስለገጠመን አስደንጋጭ ክስተት አስነብባችኋለሁ።

የዛሬ አራት ዓመት ገደማ እ አ አ በፍብሪዋሪ 2019 የድሮ አለቃዬ የነበሩትን ዶ/ር በዳዳ ግርማን ለማግኘት ወደ ቁሉምሳ አሰላ ለመሄድ ጉዞ ስጀምር በዚያን ቀን አዳማ እንዳሉ ሰለነገሩኝ እኔም ጉዞዬን ወደአሉበት ሥፍራ አደረኩ። ዶ/ር በዳዳንም የቅርብ ጓደኛቸው ከሆኑት ከዶ/ር ጀማል ጋር በዶ/ር ጀማል ቤት ሲጨዋወቱ አገኘኋቸሁ። እኔም በዚያች አጋጣሚ ለ34 ዓመታት የተለኋቸሁን ዶ/ር ጀማልን ለማግኘት ዕድሉ ገጠመኝ። በአዋሽ በረሃ ውስጥ በሚገኘዉ የመልካ ወረር እርሻ ምርምር ማዕከል የያኔዉ አቶ ጀማል ለዶክትሬታቸዉ ማሟያ ይሆን ዘንድ በቆላ ስንዴ ላይ ምርምር ሲሰሩ እኔም ከዩኒቨርስቲ በባችለር ተመርቄ በዚሁ ሰብል ላይ አብሬአቸዉ እንድሰራ የተመደብኩበት ዓመት ነበር።

የኛ ምረቃ በመደበኛዉ የምረቃ ጊዜ የተከናወነ አልነበረም። በ1977 (ወይም እ አ አ በ1984) በሀገራችን በተከሰተዉ ከፍተኛ ረሃብ መሰረት በድርቅና ረሃብ የተጎዱ ዜጎቻችንን በምዕራቡ የሀገራችን ክፍል ለማስፈር መንግሥት ባወጣዉ ዕቅድ መሰረት በሀገሪቱ ያሉ ዩኒቨርስቲዎች በሙሉ ተዘግተዉ ለሰፋሪዎች በዘመቻ ቤት እንድንሰራ ተላክን። የኛ አለማያ ኮሌጅም የካራማራ ብርጌድ ተብሎ ጋምቤላ በሚገኘዉ የጊሎ አቦል ሥፍራ ተመደብን። ለሶስት ወራት በዘመቻዉ ከቆየንና የጎደለብንን የትምህርት ክፍል ካሟላን በኋላ የተመረቅነዉ በታህሳስ 1978 (እ አ አ ዲሴምበር 1985) ነበር። በዚህ ምክንያት ነዉ እኔም ወደ አዲሱ የምርምር ማዕከሌ ስሄድ ያጋጠመኝ በመስክ ላይ ያለ የስንዴ ማሳ የሆነዉ። ያለበለዚያ በመደበኛዉ ወቅት ብንመረቅ ኖሮ የጥጥ ማሳ ነበር የሚጋጥመኝ። ምክንያቱም የስንዴ ተክል በመደበኛዉ የሰብል ወቅት ያለዉን ከፍተኛ ሙቀት መቋቋም ስለማይችል ነዉ።

ዶ/ር ጀማልም ከረጅም ጊዜ የውጭ ቆይታ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰዉ ወልጀጂ የግብርና ኢንዱስትሪ (Woljeejii Agricultural Insdustry PLC, WAI) የሚባል ጽ/ቤቱ ቢሾፍቱ የሆነ ድርጅት ከፍተዉ እ አ አ ከ2015 ጀምሮ እየሰሩ እንደሆነ ገለጹልኝ። ዶ/ር ጀማልም የድርጅቱ ማናጄርና አሰልጣኝ ሲሆኑ ድርጅታቸዉም ትኩረት አድርጎ የሚሰራዉ ጠቃሚ የሆኑ ረቂቅ ህዋሳት (effective microorganisms) ወይም በአጭሩ EM በመጠቀም ነዉ። በዚሁ መስክ በመሥራት ላይ ያሉትን ሥራቸዉን አስጎቡኝ። ይህ EM ቴክኖሎጂ በተለያዩ መስኮች ተግባራዊ ይሆናል። ከነዚህም ውስጥ የዶሮች መኖ፣ የከብቶች መኖ፣ ቆዳና ሌጦ ዝግጅት እንዲህም የአፈር ለምነት ለማሳደግ ጥቅም ላይ ይዉላል። በለተይም በዚህ መስክ የሚዘጋጁት የተለያዩ ዉጤቶች አካባቢያችንን ከመበከል የነጹ ናቸዉ ማለት ይቻላል። ዶ/ር ጀማልም ክሚመለከታችዉ መንግሥታዊ ድርጅቶች እዉቅናና ፍቃድ ተሰጥቷቸዉ ይሰሩ ነበር።

እኔም የዶ/ር ጀማል EM ቴክኖሎጂ የጤፍ ምርትን ሊያሳድግ የሚችልበትን በተለይም ዝናብ አጠር በሆኑ አካባቢዎች ጥቅም ላይ የሚዉልበትን መንገድ በጋራ ማጥናት የሚቻል ከሆነ ብዬ በጠየኳቸዉ ጊዜ ፍቃደኛ ሆነዉ በመገኘታቻዉ አዲስ ፕሮጀከት ነድፈን መንቀሳቀስ ጀምረን ነበር። EM ቴክኖሎጂ በሰብል ማሻሻያ ላይ ያለዉን አቅምና ተስፋ ወደፊት አስነብባችኋለሁ።

በጋራ ለምንሰራዉ አዲሱ ፕሮጀክታችንም የተለያዩ ግባቶችን በማጠናቀርና ከሚመለከታቸዉ ተሳታፊ ግለሰቦች መረጃዎችን በማሰባሰብ ላይ ነበርኩ። ዶ/ር ጀማልም ፌብሪዋሪ 1፣ 2021 በተጻፈ ኢሜላቸዉ ጠቃሚ መረጃዎች ልከዉልኝ ነበር።

ይህ በዚህ እንዳለ እ አ አ ማርች 2፣ 2022 (ማለትም የዛሬ 10 ወር) በተጻፈ ኢሜል ዶ/ር ጀማል በጠና እንደታመሙ ተነገረን። እኔም የዛሬ 37 ዓመት ወደ ሥራ ዓለም ስገባ የስንዴ ምርምርን ያስተዋወቁኝ እኝህ ከፍተኛ ተመራማሪን በህመማቸዉ ምክንያት ላናግራቸዉ ባልችልም ልጃቸዉንና የቅርብ ጓደኛቸዉ የሆኑትን ዶ/ር በዳዳን ለማነጋገር ቻልኩ። ዶ/ር ጀማል በሆስፒታል እርዳታ ሲደረግላቸዉ ቆይቶ እ አ አ ማርች 27፣ 2022 በተወለዱ 76 ዓመታቸዉ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩን። በ EM ቴክኖሎጂ በርካታ ሥራዎች ለመሥራት ዕቅድ የነበራቸዉ እኚህ ጠንካራ ሰዉ እስከ ወዲያኛዉ አሸለቡ።

በጋራ ልንሰራ ላቀድነዉ ፕሮጀክት ብለዉ ዶ/ር ጀማል ከሁለት ዓመት በፊት ያጋሩኝን አጭር የህይወት ታሪካቸዉን ከዚህ በታች አቀርባለሁ።

የትዉልድ ጊዜ፤ ሜይ 18፣ 1946 (እ አ አ)

የትዉልድ ሥፍራ፤ ጎሬ

የትምህርት ዝግጁነት

  • ዲፕሎማ (1967 እ አ አ) በአጠቃላይ እርሻ፤ ከጂማ የእርሻና ቴክኒክ ት/ቤት
  • ባችለር (1972 እ አ አ) በዕጽዋት ሳይንስ፤ ከእርሻ ኮሌጅ፣ ቀደማዊ ኃይለ ስላሴ ዩኒቨርስቲ
  • ማስትሬት (1977 እ አ አ) በዕጽዋት ማዳቀል፡ ከኖርዝ ካሮሊና ዩኒቨርሲቲ፣ አሜሪካ
  • ፒ ኤች ዲ (1989 እ አ አ) በዕጽዋት ማዳቀልና አግሮኖሚ፤ ዩስቲስ ሊቢግ ዩኒቨርስቲ፣ ጀርመን

የሥራ ልምድ

  • 1972 – 1989 (እ አ አ) ተመራማሪ፤ በእርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት
  • 1989 – 1991 (እ አ አ) ከፍተኛ ተመራማሪ፤ ዩኒቨርስቲ ኦፍ ናይሮቢ፣ ኬንያ
  • 1991 – 1997 (እ አ አ) ከፍተኛ ሌክቸረር፤ ናሽናል ዩኒቨርስቲ ኦፍ ሌሴቶ
  • 1997 – 2015 (እ አ አ) ተባባሪ ፕሮፈሰር፤ ናሽናል ዩኒቨርስቲ ኦፍ ሌሴቶ
  • 2015 – 2022 (እ አ አ) ማናጄር እና አሰልጣኝ፤ WAI አዳማ

በማስተማር መስክ፤ የተለያዩ ኮርሶችን በዩኒቨርስቲ ደረጃ አስተምረዋል

በምርምር መስክ፤ በተለያዩ ሰብሎችና ሀገሮች የተሳተፉ ሲሆን እነዚህም ስንዴ፣ ማሽላ እና ድንችን ያካትታል

ያጸድቋቸዉ ዝርያዎች ብዛት፤ 9 (ስንዴ፣ ማሽላ፣ በቆሎ፣ ነጭ ሽንኩርት)

የማማከር ሥራ፤ በርካታ ናቸዉ

በሥራቸው ምክንያት የጎበኟቸዉ ሀገራት ብዛት፤ 26

ያሳተሟቸዉ ጽሑፎች ብዛት

  • 11 ቴክኒካል ሪፖርቶች
  • 13 የጆርናል ወረቀቶች
  • 22 የኮንፈረንስ ወረቀቶች

በዚሁ ስለ ዶ/ር ጀማል የጻፍኳቸዉን ብሎጎቼን አበቃለሁ።

ለወዳጆቻቸዉና ዘመዶቻቸዉ መፅናናትን እመኛለሁ።

በሌላ ጽሑፍ እስከምንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 17 ቀን 2015 ዓ.ም. (December 26, 2022)

ግብርናችንን ለማዘመን፤ የቆላ ስንዴን በመስኖ ያስተዋወቁን ፤ ዶ/ር ጀማል መሐመድ፤ ክፍል 2

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የቆላ ስንዴን በመስኖ ያስተዋወቁን ፤ ዶ/ር ጀማል መሐመድ፤ ክፍል 2

በክፍል 1 ጽሑፌ መስኖን በመጠቀም የቆላ ስንዴ ምርምር በመካከለኛዉ አዋሽ በተለይም በመልካ ወረር እርሻ ምርምር ማዕከል ስለ አስጀመሩልን ስለ ዶ/ር ጀማል መሐመድ አስተዋጽኦ በአጭሩ ዘግቤ ነበር። ጊዜዉ ከዛሬ 37 በፊት እ አ አ በ1985 ነዉ። ዶ/ር ጀማል ለሶስተኛ ዲግሬቸዉ ማሟያ የሚሆን የምርምር ሥራቸዉን የሚሰሩበት ዓመት ሲሆን እኔም በባችለር ዲግሪ ተመርቄና በእርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት ተቀጥሬ ወደ መልካ ወረር እርሻ ምርምር ማዕከል የተቀላቀልኩበት ዓመት ነበር። በማዕከሉም የስንዴ አግሮኖሚስት በመሆን ከዶ/ር ጀማል ጋር በቅርበት እንድሰራ ተመደብኩ። በሕይወቴ የመጀመሪያውን የምርምር ሥራ የጀመርኩትም በዚሁ የስንዴ ምርምር ላይ ስለነበረ በዚያ የወረር ሞቃታማ አየር ቀኑን ሙሉ ሜዳ ላይ ስንሰራ የነበረዉ የሥራ ፍቅር እስካሁንም ድረስ ትዝ ይለኛል።

ዶ/ር ጀማል የምርምር ዉጤታቸዉን Potentials and Possibilities of Double Cropping Wheat After Cotton Under Irrigation in Awash Valley, Ethiopia. በሚል የፒ ኤች ዲ ቴሲሳቸዉን እ አ አ በ1989 ጀርመን ሀገር ጊሴን በሚገኘዉ የዩስቱስ ሊቢግ ዩኒቨርስቲ አሳትመዋል።

ከዚሁ የቆላ ስንዴ ምርምር ዉጤታቸው ጋር በተገናኘ በርካታ ጽሑፎችንም አሳትመዋል። እነዚህ ጽሑሁፎችም በሳይንሳዊ ጆርናል የታተሙና በፕሮሲዲንግ የታተሙ ተብለዉ ለሁለት ሊከፈሉ ይችላሉ።

በሳይንሳዊ ጆርናሎች ከታተሙት ውስጥ በቆላ ስንዴ ምርምር ላይ ካተኮሩት ውስጥ የሚከተሉት ይገኙበታል።

  • Jamal Mohammed. 1985. Effects of sowing dates and seedbed preparation methods on yield of wheat. Ethiopian Journal of Agricultural Sciences 7(2): 81-88
  • Jamal Mohammed. 1992. Selection and evaluation of potential wheat for double cropping under irrigation in Awash Valley, Ethiopia. Tropical Agriculture 69: 186-190.
  • Jamal Mohammed. 1994. Responses of wheat cultivars to dates of sowing under irrigation in Ethiopia. Uniswa Journal of Agriculture 3: 5-13
  • Jamal Mohammed 1994. Performance of wheat genotypes under irrigation in Awash Valley, Ethiopia. African Crop science Journal 2: 145-151

ዶ/ር ጀማል በዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶች ላይ ካቀረቧቸዉ ጽሑፎች መካከል የቆላ ስንዴ ምርምርን በተመለከተ በፕሮሲዲንጎች ከታተሙት የሚከተሉት ይገኙበታል።

  • Jamal Mohammed. 1987. Recommended cultural ppractices for irrigated wheat in the Middle Awash valley. In: Proceedings of the 19th National Crop Improvement Conference. IAR, Addis Ababa, Ethiopia.
  • Jamal Mohammed. 1987. Increasing wheat Production in Ethiopia by introducing double cropping under irrigation. In: Proceedings of the 5th Regional Wheat Workshop for Eastern, Central and Southern Africa. CIMMYT, Mexico. pp. 161-165.
  • Tilahun Hordofa, Tadele Gebreselassie and Jamal Mohammed. 1987. Optimum irrigation frequency and amount for wheat in the Middle Awash Valley. In: Proceedings of the 19th national Crop Improvement Conference. IAR, Addis Ababa, Ethiopia.
  • Jamal Mohammed. 1991. Irrigated wheat potential in Awash Valley, Ethiopia. In: Proceedings of the 7th Regional Wheat Workshop for Eastern, Central and Southern Africa, Nakuru, Kenya.
  • Jamal Mohammed. 1993. Wheat as a second crop for off-season production after cotton in the Awash Valley, Ethiopia. In: Proceedings of the First Crops Sciences Conference for Eastern and Southern Africa, Kampala, Ethiopia.

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት የዶ/ር ጀማል ጽሑፎች የቆላ ስንዴን በመስኖ ለሚያለሙ ጠቃሚ መረጃዎች ናቸዉ። በተለይም በዓመት ሁለት ሰብሎችን ለማምረት በሚደረገዉ እንቅስቃሴ ላይ ለሚሳተፉት ዝርያን፣ የመሬት ዝግጅትን፣ የዘር መጠንን፣ የመዝሪያ መንገድ፣ ወ ዘ ተ በምርምር ላይ የተመርኮዘ ጽሑፎች ማግኘት ይቻላል።

በክፍል 3 ጽሑፌ ከዶ/ር ጀማል ጋር ባለፉት ጥቂት ዓመታት በጋራ ልንሰራ ስላቀድነዉ ልዩ የምርምር ፕሮግራም አስነብባችኋለሁ።

እስከዚያው መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ታህሳስ 17 ቀን 2015 ዓ.ም. (December 26, 2022)