ግብርናችንን ለማዘመን፤ የጤፉ ጠቢብ፣ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ፤ ክፍል 1

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሑፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

የጤፉ ጠቢብ፣ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ፤ ክፍል 1

በዛሬዉ ጽሑፌ በግብርናዉ መስክ ከፍተኛ ዕዉቀትና የሥራ ልምድ ስላካበቱትና በተለይም በጤፍ ላይ ላለፉት 40 ዓመታት በምርምርና ልማት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ ስላሉት ስለ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ አስነብባችኋለሁ፡፡ የጤፉ ጠቢብ የሚል መጠሪያ የሰጠኋቸዉም እስካሁን ድረስ ከነበሩት የጤፍ ተመራማሪዎች መካከል እንደ ዶክተር ክበበዉ ለረጅም ጊዜ በአንድ ሰብል ላይ የሰራ ወይም ያገለገለ ስላላጋጠመኝ ነዉ። ምናልባትም በሀገራችን ካሉ ተመራማሪዎች ሁሉ በአንድ ሰብል ላይ ብቻ ለረጅም ጊዜ በማገልገል ዶክተር ክበበዉ ግንባር ቀደም እንደሚሆኑ አልጠራጠርም።

በነሐሴ 22 ቀን 1951 (እ አ አ ኦጎስት 28፣ 1959) አርሲ ውስጥ በምትገኘዉ ሁሩታ የተወለዱት ዶክተር ከበበዉ የመጀመሪያ ዲግሪያቸዉን ካገኙበት እ አ አ 1983 ጊዜ ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ቢሾፍቱ በሚገኘዉ የደብረ ዘይት ግብርና ምርምር ማዕከል በማገልገል ላይ ይገኛሉ።

ምስሉ የሚያሳየዉ እ አ አ በ2012 በደብረ ዘይት ግብርና ምርምር ማዕከል በተዘጋጀዉ አጭር ሥልጠና ላይ ተሳታፊዎችን የሚያሳይ ሲሆን ዶክተር ክበበዉ (ከፊት ረድፍ ካሉት ከግራ ወደ ቀኝ አራተኛዉ) ሥልጠናዉን ከሰጡት መካከል አንዱ ነበሩ፡

ከዚህ በታች የዶክተር ክበበዉ አሰፋን የትምህርት ዝግጁነትና የሥራ ልምድ እንዲሁም አስተዋጽኦ በአጭሩ አቀርባለሁ፡፡

የትምህርት ዝግጁነት

  • ፒ ኤች ዲ፣ እ አ አ በ2003፣ በዕጽዋት ቢሪዲንግ እና ጄኔቲክስ፣ ከስዊዲሽ ዩኒቨርስቲ ኦፍ አግሪከልቸራል ሳይንስ፣ ስዊድን
  • የሁለተኛ ወይም የማስተር ዲግሪ፣ እ አ አ በ1991፣ በአግሮኖሚ፣ ከሃረማያ ግብርና ዩኒቨርሲቲ፣ ኢትዮጵያ
  • የመጀመሪያ ዲግሪ፣ እ አ አ በ1983፣ በዕጽዋት ሣይንስ (በማዕረግ)፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፣ ኢትዮጵያ
  • የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት፣ እ አ አ በ1979፣ ከአሰላ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፣ አሰላ
  • የመጀመሪያ እና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት፣ እ አ አ በ1973፣ ከንጉሥ ሐይለመለኮት ትምህርት ቤት፣ ሁሩታ

ተጨማሪ ሥልጠናዎች

  • ሙቴሽን ቢሪዲንግ ለሰብል ማሻሻያ (Mutation for Crop Improvement)፣ ለአንድ ዓመት እ አ አ 1994/95፣ ሲሌሲያን ዩኒቨርስቲ፣ ፖላንድ
  • ፕሮጀክት ዲዛይን፣ ለአንድ ወር እ አ አ በ1993፣ ዩኒቨርስቲ ኦፍ አምስተርዳም

የሥራ ልምድ (በከፊል)

  • መሪ ተመራማሪ (Lead Researcher)፣ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት፣ እ አ አ ከ2017 አንስቶ እስከ አሁን
  • ከፍተኛ ተመራማሪ፣ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት፣ ደብረ ዘይት ምርምር ማዕከል፣ እ አ አ አ ከ2004 እስከ 2017
  • ረዳት ፕሮፌሰር፣ ሃረማያ ዩኒቨርስቲ፣ እ አ አ ከ2003 እስከ 2004
  • ሌክቸረር፤ ሃረማያ ዩኒቨርስቲ፣ እ አ አ ከ1985 እስከ 2003

በኃላፊነት የሰሩባቸዉ ቦታዎች (በከፊል)

  • መሪ ተመራማሪ (Lead Researcher)፤ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት፤ እ አ አ ከ2017 አንስቶ እስከ አሁን
  • ዋና ተመራማሪ (Principal Investigator)፤ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩትና የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኤጄንሲ ፕሮጀከት፤ እ አ አ ከ2015 እስከ 2017
  • አስተባባሪ፤ የብሔራዊ የጤፍ ፕሮግራም፤ እ አ አ ከ2008 አንስቶ እስከ 20018
  • ዳይሬክተር፤ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የደብረ ዘይት ምርምር ማዕከል፤ እ አ አ ከ2006 እስከ 2009
  • ብሔራዊ አስተባባሪ እና ዋና ተመራማሪ፤ ትኩረቱን በሽንብራ ላይ ያደረገዉ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት እና የኢክሪሳት ትብብር ፕሮጀክት፤ እ አ አ ከ2007 እስከ 2009
  • ዋና ተመራማሪ፤ በጤፍ ምርምር ትኩረት ያደረገ የማክናይት ትብብር ፕሮጀክት

ምስሉ የሚያሳየዉ እ አ አ በ2019 በተካሄደዉ ሶስተኛዉ ዓለም አቀፍ የጤፍ ኮንፈረንስ ላይ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ሲያደርጉ ነዉ፡፡ ፎቶ፣ ዘሪሁን ታደለ፡፡

ያሳተሟቸዉ ጽሑፎች፤ በአጠቃላይ 150 ሲሆኑ ከነዚህ ዉስጥ 100 የሚሆኑት በሳይንሳዊ ጆርናሎች የታተሙ ናቸዉ፡፡

የተሻሻሉ የጤፍ ዝርያዎች ማጸደቅ፤ በሀገራችን የተለያዩ ወካይ አግሮኢኮሎጊዎች ተገምግመዉ እንዲጸድቁ ከተደረጉት የጤፍ ዝርያዎች መካከል ዶክተር ክበበዉ በአብዘኛዎቹ ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ተሳትፈዋል፡፡

የተበረከተላቸዉ ሥጦታዎች ወይም ዕውቅናዎች (በከፊል)

  • የዕድሜ ልክ የስኬት ሽልማት (Life Time Achievement Award)፤ በኢትዮጵያ የሰብል ሣይንስ ባለሙያዎች ማህበር፤ ለሰብል ሣይንስ ምርምር እና ልማት ላደረጉት የላቀ አስተዋጽኦ፤ እ አ አ ፌብሪዋሪ 2023
  • የኢትዮጵያ ስጦታ (Gifts of Ethiopia Award)፤ በዋን ኦፍ ዘጊፊት ኦፍ ኢትዮጵያ አዋርድ የጤፍ ምርምር እና ልማትን ለማስፋፋት ላደረጉት ቁርጠኝነት፤ እ አ አ ዲሴምቤር 2021
  • ከፍተኛ የክብር ተሸላሚ (Higher Honor Laureate)፤ የአብሲኒያ ሽልማት፤ የእድሜ ልክ የግብርና ምርምር ምድብ፤ እ አ አ 2019
  • ባልደረባ (Fellow)፤ የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ፤ እ አ አ ከ2015 ጀምሮ
  • የብሔራዊ ሽልማት፤ ለጤፍ ምርምር ቡድን፤ በጤፍ ምርምር ላገኙት ከፍተኛ ግኝት በተለይም የቁንጮ ዝርያ ቴክኖሎጂን በሚመለከት፤ በኢትዮጵያ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፤ እ አ አ በ2012

ምስሉ የሚያሳየዉ እ አ አ በፌብሪዋሪ 2023 በተካሄደዉ የኢትዮጵያ የሰብል ሳይንስ ባለሙያዎች ኮንፈረንስ ላይ ለዶክተር ክበበዉ አሰፋና ዶክተር በዳዳ ግርማ የህይወት ዘመን ዕዉቅና ሽልማት (Life Time Achievement Award) የተሰጠበት ሥነ ሥርዓት ነዉ፡፡ ከግራ ወደ ቀኝ ዶክተር በዳዳ ግርማ፣ ዶክተር ድሪባ ገለቲ፣ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ፣ ዶክተር ታዬ ታደሰ እና ዶክተር ካሳዬ ቶለሳ፡፡ ፎቶ ዘሪሁን ታደለ፣ የካቲት 17 ቀን 2015።

ከላይ እንደተገለጸዉ ዶክተር ክበበው በርካታ አስተዋጽዎችን ማድረጋቸዉ ብቻ ሳይሆን ለነዚህ የላቁ አስተዋጽዎችም በርካታ ስጦታዎችንና ዕዉቅናዎችን አግኝተዋል።

በክፍል 2 ጽሑፌ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ በጤፍ ምርምር እና ልማት ላይ ያደረጉትን አስተዋጽኦ በሚመለከት ለቃለ መጠይቄ የሚሰጡኝን እጽፋልሁ፡፡ እስከዛዉ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መጋቢት 19 ቀን 2015 ዓ.ም. (March 28, 2023)

አስተያየት ያስቀምጡ