ግብርናችንን ለማዘመን፤ የባህር አረም ሰብሎቻችንን ለማንቃትና ምርት ለማሳደግ ያለዉ ሚና

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ፡፡

የባህር አረም ሰብሎቻችንን ለማንቃትና ምርት ለማሳደግ ያለዉ ሚና

የባህር አረም ብዬ የተጠቀምኩት በእንግሊዘኛ seaweed ተብለዉ የሚታወቁትንና በባህር ውስጥ የሚያድጉትን የተለያዩ የአልጌ (algae) ዓይነቶችን የሚካትተዉን ለማሳየት ነዉ። እንዚህ የባህር አረሞች ከዚህ በታች በሚታዩት ምስሎች ይወከላሉ።

ምስሎቹ የሚያሳዩት የባህር አረም ከባህር ሥር እንዴት እንደሚያድግ (በስተግራ) እና በተናጠል ያለ የባህር አረምን ነዉ። ምንጭ፤ https://businesswales.gov.wales/farmingconnect/news-and-events/technical-articles/seaweed-agriculture (በስተግራ ላለዉ) https://stock.adobe.com/search?k=seaweed (በስተቀኝ ላለዉ)

መረጃዎች እንደሚያሳዩት እነዚህ የባህር አረሞች ተብለዉ የሚጠሩት ተክሎች ለበርካታ አገልግሎት ጥቅም ላይ ይዉላሉ። እነዚህም ለሰዉ እና ለእንስሳት ምግብነት፣ ለመዲሃኒትነት፣ ለማዳበሪያ፣ ለተለያዩ የፋብሪካ ግባቶች፣ ወዘተ ናቸዉ። ለሰዉ ምግብነት በተለያዩ መልኮች ያገለግላል። ለምሳሌ እንደ ሾርባ፣ ብስኩት፣ ሻይ ቅጠል፣ ወዘተ በመሆን ጥቅም ላይ ይዉላል። እኔም የዛሬ 25 ዓመት ገደማ የሥራ ባልደረባዬ የነበረዉ ጃፓናዊ ሳይንቲስት በተለያየ ወቅት ከሀገሩ የሚያስመጣዉን ከባህር አረም የሚሰሩ የተለያዩ ብስኩቶችን ያጋራኝ ነበር። በሀገሩ በጣም ተወዳጅ እንደነበሩም ይነግረኝ ነበር።

በዛሬዉ ጽሑፌ ትኩረት የማደርገዉ ይኸዉ የባህር አረም በግብርና መስክ ስለሚሰጠዉ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በተለይም ሰብሎቻችንን እንደ አነቃቂ ወይም አንቂ ሆኖ በማገልገል ምርት እንዲያድግ በሚያስችለዉ ላይ ነዉ።

ከታች በምስሉ እንደሚታየዉ የባህር አረም በርካታ ምርትን ለማሳደግ የሚረዱ የአፈርና የተክል ባህርያትን ለማሻሻል ይችላል። ለዚህም ነዉ አንቂ ወይም Biostimulant የሚለዉ ስም የተሰጠው። የምርት መጠን ብቻ ሳይሆን ጥራትንም በማሳደግ ጉልህ አስተዋጽኦ ያደርጋል። የሚገርመዉ በሌሎች መስኮች ካለዉ ጥቅም በተጨማሪ በሰብሎቻችን ላይ ይህ የባህር አረም ያለዉ ጉልህ አስተዋጽኦ ያስደንቃል። ስለዚህ የባህር አረም ሰብሎቻችን ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችን ከአፈር ውስጥ እንዲያገኙ ማመቻቸት ብቻ ሳይሆን ሰብሎቻችን ለድርቅና ጨዋማ አፈር በተጋእጡ ጊዜም እነዚህን አስቸጋሪ ክስተቶች እንዲቋቋሙ ይረዷቸዋል።

ምስሉ የሚያሳየዉ ከባህር አረም የሚቀመመዉ በፈሳሽም ሆነ በፓዉደር መልክ የሚዘጋጀዉ ለአፈር ለምነትና እና የተክል ዕድገት ጠቃሚ መሆኑን ነዉ። + ሚለዉ ምልክት የሚያሳየዉ የባህር አረም ሰብላችንን ለማሻሻል ወይም  አፈራችንን ለማበልጸግ ጠቃሚ እንደሆነ ነዉ። በዚሁ መሠረት የባህር አረም ከላይ ለተገለጹት ባህርያት ጥቅም ይሰጣል። ምንጭ፤ Plants (2020) 9: 359. doi: 10.3390/plants9030359

ምንም እንኳ የባህር አረም እነዚህን በርካታ የተክልና የአፈር ባህርያትን ለማሻሻል እንደ አንቂ ሆኖ ቢያገልግልም እንዴት እነዚህን ሁሉ ሚናዎች ሊጫወት እንደቻለ ገና በጥናት ላይ ነዉ። አንደ አንዳንድ  ተመራማሪዎች ግምት የባህር አረም በዉስጡ የተለያዩ ፖሊሳካራይድ፣ ፌኖል እና ሆርሞኖችን የያዘ በመሆኑ እነዚህ ንጥረ ነገሮች እንደ አንቂ ሆነዉ ሊያገለግሉ እንደሚችሉ ነዉ። በአሁኑ ጊዜ ተመራማሪዎች የባህር አረምን ጥቅም በተለያዩ ሰብሎች እየፈተሹ ይገኛሉ። እንዴትስ በተመጣጣኝ ወጪ ጥቅም ላይ የሚዉልበትን መገድም ያጠናሉ።

ማጠቃለያ

የባህር አረም በሚል ስም የተሰሙት የተክል ዓይነቶች በርካታ ከመሆናቸዉ በላይ በባህር ዉስጥ ብቻ ሳይሆን በሐይቆችና ወንዞችም ጭምር የሚያድጉ ስለሆነ በጥቅም ላይ ልናዉላቸዉ የምንችልበትን መንገድ መፈለግ ይኖርብናል። ምንም እንኳ ስለሚመረትበት ሥፍራ መረጃ ባላግኝም እ አ አ በ 2012 ኢትዮጵያ የባህር አረምን ኤክስፖርት በማድረግ ወደ ሶስት ሚሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገቢ አግኝታለች። የመረጃዉ ምንጭ፤https://www.selinawamucii.com/insights/prices/ethiopia/seaweed/

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ ድረስ መልካሙን እመኛለሁ። ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ የካቲት 5 ቀን 2015 ዓ.ም. (February 12, 20

አስተያየት ያስቀምጡ