ግብርናችንን ለማዘመን፤ የከተማ ግብርና

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የከተማ ግብርና

ግብርና የተለመደዉ በገጠር ቢሆንም ባንዳንድ የዓለማችን ክፍሎች መጠነ-ሰፊ ግብርና በከተሞችም ይካሄዳል። እነዚህ የከተማ እርሻዎች የተለያዩ ሰብሎችን የሚያመርቱ ሲሆን ለምግብነት የሚዉሉ እንስሳዎችንም ያረባሉ። በተለይም በአትክልትና ፍራፍሬ ላይ ያተኮረ የከተማ ግብርና ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶታል። በዓለማችን ወደ 800 ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ በከተማ ግብርና እንደሚሳተፍ ይገመታል

የተባበሩት መንግሥታት የምግብና እርሻ ድርጅት ሪፖርት እንደሚያሳየዉ የሰብል ከወሰድን የከተማ ግብርና ገጠር ካለዉ ግብርና እስከ 15 እጅ የበለጠ ምርታማ ነዉ። በሪፖርቱ መሠረት ከአንድ ካሬ ሜትር የከተማ ቦታ እስከ 20 ኪሎ ግራም ምግብ ማምረት ይቻላል። በዚሁ መሠረት አንዳንድ የዓለማችን ከተሞች የከተማ ግብርናን አስፋፍተዉ ይገኛሉ። በከተሞች ዉስጥ የመሬት ጥበት በመኖሩ ምክንያት የከተማ ግብርና በመሬት ላይ ብቻ ሳይሆን በህንፃዎች ጣራ ላይም በሰፊዉ ተግባራዊ እየሆነ ይገኛል።  ለምሣሌ የፓሪስ ከተማ ከሶስት ዓመት በፊት እ.ኤ.አ. በ2016 በነደፈዉ ዕቅድ መሠረት በአራት ዓመት ዉስጥ 100 ሄከታር የሚሸፍን በቤቶች ጣራ ላይ የሚመረት አትክልት ለማልማት አቅዶ ነበር። በዚህ ተግባሯም ከተማዪቱ በዓለማችን ታዋቂነትን አትርፋለች። ይህችዉ ከተማ በአሁኑ ዓመት ደግሞ 32 አዳዲስ የከተማ ግብርና ሥፍራዎችን አስጀምራለች። ስለዚህ እንደ ቲማቲም፣ ጎመን፣ ሰላጣ፣ ካሮት፣ ሃባብ፣ ወዘተ በቤታቸዉ ጣራ ላይ በማምረት ከራሳቸዉ ፍጆታ አልፈዉ ለሽያጭም የሚያቀርቡ የከተማ ገበሬዎች ብቅ እያሉ ነዉ። በተለይ ይህ ተግባራዊ ሊሆን የሚሆነው የህንፃቸዉ ጣራ ጠፍጣፋ የሆነ እንደሆነ ነዉ።

ከላይ በምሥሉ የሚታየዉ ፉኩኦካ በምትባል የጃፓን ከተማ በሚገኝ ህንፃ ላይ የለማ እርሻ ሲሆን ለህንፃውም መልካም ዉበት አሰጥቶታል። ምሥሉ የተወሰደዉ ከዚህ ድህረ ገጽ ነዉ።

በኢትዮጵያ የከተማ ግብርና በሰፊዉ ተስፋፍቶ ባይገኝም ባንዳንድ ክፍት ቦታዎችና የመስኖ ዉሃ በሚደርስባቸዉ ሥፍራዎች የጓሮ አትክልቶች ሲተከሉ የታያል። ለምሣሌ በአዲስ አበባ የትንሿ አቃቂ ወንዝን በመጠቀም በመካኒሣ፣ ጎፋና ላፍቶ የተወሰኑ እርሻዎች ነበሩ። ቴዎድሮስ ፊርዲሳ የተባሉ ለማስተርት ዲግሪ ለሚያበቃቸዉ ያደረጉት ጥናት እንደሚያሳየዉ እ.ኤ.አ. በ2007 በአዲስ አበባ ውስጥ ካሉት 10 ክፍለ ከተሞች ዉስጥ ሰባቱ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን የከተማ ግብርና ያካሄዱ ነበር። የከተማ ግብርናን የማያካሂዱት ሶስቱ ክፍለ ከተሞች አዲስ ከተማ፣ አራዳና ቂርቆስ ናቸዉ።

በከተማ ግብርና የተለመዱትን የአትከልትና ፍራፍሬ ዓይነቶች ብቻ ሳይሆን እንደ እንጉዳይ የመሳሰሉትንም በማሳደግ የአመጋገብ ሥርዓታችንን ማስፋት ብቻ ሳይሆን እንደ ገቢ ምንጭነትም ልንጠቀምበት እንችላለን። ጠቃሚ ከሆኑ የምግብ ንጥረ ነገሮች መካካል እንጉዳይ በቂ የሆነ ፕሮቲን፣ ቫይታሚን ቢ፣ ቫይታሚን ሲ፣ ካልሺየም፣ ወዘተ በውስጡ ይዟል። ከዚህ በተጨማሪ ሴሎቻችንን ከተለያዩ የበሽታ ጥቃቶች ሊከላከልን ይችላል ተብሎ የሚገመተዉ ሴሊኒየም የተባለ ንጥረ ነገር እንጉዳይ ከሌሎች ተክሎች በተሻለ ሁኔታ በዉስጡ ይዟል።.

በዓለማችን የተለያዩ ዓይነት የእንጉዳይ ዓይነቶች ያሉ ሲሆን ጥቅማቸዉም እንዲሁ የተለያየ ነዉ። ከምግብ በተጨማሪ ለመድሃኒትነትም ያገለግላል። ለምሳሌ በአይጦች ላይ የተደረገዉ ሙከራ እንደሚያሳየዉ ፒዮፒኖ የተባለዉ የእንጉዳይ ዓይነት የካንሰር በሽታን እንዳይስፋፋ ከማድረጉም በተጨማሪ የስኳር በሽታ ባለባቸዉ አይጦች ወስጥ በደማቸዉ ዉስጥ ያለዉ የስኳር መጠን ከሚፈለገዉ በላይ እንዳይጨምር ሊቆጣጠር ችሏል

የእንጉዳይ እርሻ ትንሽ ቦታ የሚጠይቅ ሲሆን ሰብሉም በማንኛዉም የአየር ንብረት ጊዜ ሊመረት ይችላል። ምክንያቱም በቤት ውስጥ ስለሚተከል ተለዋዋጭ ከሆነ የአየር ንብረት ከለላ ይኖረዋል ማለት ነዉ። ከእንጉዳይ እርሻ የሚገኘዉ ምርትም ከፍ ያለ ነዉ።  ለምሳሌ በ10 ካሬ ሜትር ላይ ካለ የእንጉዳይ እርሻ እስከ 10 ኪሎ ግራም እንጉዳይ ማምረት የሚቻል ሲሆን ከተተከለበት እስክሚታጨድበት በጠቅላላ የሚፈጀዉ ከሶስት እስከ አራት ሣምንታት ብቻ ነዉ

በኢትዮጵያም እንጉዳይን በተመለከተ የተወሰኑ ጥናቶች ተካሂደዋል። እንደ ቀርቅሃ ከመሳሳሉ ቁሳቁሶች እንጉዳይ የሚያድግበት ቤት ለመሥራት እንደሚቻል እነዚሁ ጥናቶች ያስረዳሉ። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባልደረባ የሆኑት ዶክተር አሻግሬ ዘዉዱ ለዶክትሬት ተምህርታቸዉ ማሟያ Laetiporus Sulphureus በሚባለዉ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ለመዲሃኒትነት በሚያገለግለዉ የእንጉዳይ ዓይነት ላይ ጥናት አካሂደዋል። ቢሆንም የእንጉዳይ እርሻም ይሁን አመጋገብ በሀገራችን በሚፈለገዉ ደረጃ ያደገ አይደለም ብል የተሳሳትኩ አይመስለኝም። ስለዚህ እንጉዳይ ከሌሎቹ የወጥ ዓይነቶች ጋር በማዕዳችን የሚሰለፍበት ጊዜ ይመጣል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።

ምሥሉ የሚያሳየዉ በደህና ሁኒተአ ያደገ እንጉዳይ ነዉ። ምሥሉ የተገኘዉ ከዚህ ድህረ ገጽ ነዉ።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ሐምሌ 5፣ 2011 ዓ.ም. (July 12, 2019)

One thought on “ግብርናችንን ለማዘመን፤ የከተማ ግብርና

አስተያየት ያስቀምጡ