ግብርናችንን ለማዘመን፤ ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽኦ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት

ቦሾፍቱ የተካሄደዉ ሦስተኛዉ ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት መሪ ቃል “የጤፍ ምርምርና ልማት፣ ከዬት ወደ የት?” የሚል ነበር።

ሦስተኛዉ ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት ከጥቅምት11 እስከ 13 ቀን 2012 ዓ.ም. (እ. ኤ. አ. ኦክቶበር 22 እስከ 24፣ 2019) ቢሾፍቱ በሚገኘዉ አዱላላ ሪዞርት ተካሂዷል። ለማስታወስ ያህል የመጀመሪያዉ ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት የተካሄደዉ እ. ኤ. አ. ከኦክቶበር 16 እስከ 19, 2000 በአዲስ አበባ ሲሆን ሁለተኛዉ ደግሞ የዛሬ ስምንት ዓመት እ. ኤ. አ. ኖቮምበር 7 እስከ 9, 2011 በቢሾፍቱ ነበር። በአሁኑ ሦስተኛዉ ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት ላይ በአጠቃላይ ወደ 170 የሚጠጉ ተመራማሪዎች፣ የልማት ሠራተኞች፣ ገበሬዎች፣ እንዲሁም ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።

ከኢትዮጵያ ውጭ በጤፍ ላይ በአሁኑ ጊዜ ምርምር በማድረግ ላይ ያሉና በቅርቡ ወደ ጤፍ ምርምር ለመግባት በዕቅድ ላይ ያሉ ተመራማሪዎችና ምርምርሩን በመዋዕለ ንዋይ በመርዳት ላይ የሚገኙ አካላትም ተገኝተዋል። ከእነዚህ ከዉጭ ሀገር ከመጡ ተሳታፊዎች መካከል ከአሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ጃፓን፣ ስዊዘርላንድ፣ እስራኤል እና ኬንያ የመጡ እንግዶች ይገኙበታል። በዚሁ ለሦስት ቀናት በቆየዉ አዉደ ጥናት ላይ ጤፍን በሚመለከት በተለያዩ መስኮች የተደረጉ የምርምር ዉጤቶች ቀርበዉ ውይይት ተደርጎባቸዋል።

አዉደ ጥናቱን በንግግር የከፈቱት የግብርና ሚኒስትሩ የተከበሩ አቶ ኡመር ሁሴን ሲሆኑ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት ደግሞ የእርሻ ምርምር ኢንቲትዩቱት ዳይሬክቴር ጄኔራል ዶክተር ማንደፍሮ ንጉሤ ናቸዉ። የአዉደ ጥናቱን ዓላማና ፕሮግራም ያስተዋወቁት ደግሞ ዶክተር ክበበዉ አሰፋ ናቸዉ። ዶክተር ክበበዉ ላለፉት 36 ዓመታት በጤፍ ላይ ምርምር በማድረግ ላይ የሚገኙ አንጋፋ ተመራማሪ ናቸዉ። በዚሁ የመክፈቻ ፕሮግራም ላይ የኢትዮጵያ ትራንስፎርሜሽን ኤጄንሲ እና የሲንጄንታ ፍዉንዴሽን ተወካዮች በየተራ አጠር ያለ ንግግር አድርገዋል።

ሦስተኛዉን ዓለም አቀፍ የጤፍ አዉደ ጥናት የከፈቱት የግብርና ሚኒስትሩ የተከበሩ አቶ ኡመር ሁሴን (በስተግራ) እና የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የእርሻ ምርምር ኢንቲትዩቱት ዳይሬክቴር ጄኔራል ዶክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (በስተቀኝ)።

በአዉደ ጥናት ላይ ጠቋሚ ንግግር (key note address) እንዲያደርጉ የተጋበዙት ደግሞ በጤፍ ላይ በርካታ የምርምር ዉጤቶችን ያበረከቱት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲዉ ፕሮፌሰር እንዳሻዉ በቀለ ናቸዉ። ፕሮፌሰር እንዳሻዉ “Tef: past, present and future” በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጽሑፋቸዉ በርካታ ነጥቦችን ዘርዝረዋል። ከነዚም ዉስጥ ኢትዮጵያ ጤፍን ለዓለም በስጦታ ያቀረበች ሰብል ነዉ ብለዋል። የጤፍ ምርምርንም አሁን ከሚገኝበት ደረጃ በተሻለ ሁኔታ ማሳደግ አለብን ብለዋል።

በአዉደ ጥናቱ የቀረቡት የምርምር ጽሑፎች በስድስት ክፍሎች ተከፍለዉ የቀረቡ ሲሆን በጤፍ ላይ የተሠሩ ሥራዎች በሙሉ የተዳሰሱ ነበር ማለት ይቻላል። ከዚህ በተጨማሪ በጤፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ከሚገኙ ገበሬች መካከል ወ/ሮ በቀለች ቶላ፣ አቶ ሲሳይ (ከቦሰት ወረዳ)፣ እና አቶ አምሀ አብርሃም (ከአሙሪ የዘር ድርጅት) በየተራ ንግግር አድርገዋል።

ስድስቱ ክፍሎች ሀ) አግሮኢኮሎጂና የዘር ሲስተም፣ ለ) ጄኔቲክስና ብሪዲንግ፣ ሐ) ጄኖሚክስና ባዮቴክኖሎጂ፣ መ) አፈርና ሰብል እንክብካቤ፣ ሠ) ሰብል ጥበቃ እና ረ) ሶሺዮ ኢኮኖሚክስ እና ኢክስቴንሽን ሲሆኑ በአጠቃላይ 24 ጽሑፎች ቀርበዋል።

የአዉደ ጥናቱን ዓላማና ፕሮግራም ያስተዋወቁት  ዶክተር ክበበዉ አሰፋ (በስተግራ) እና ሲንጄንታ ፍዉንዴሽንን በመወከል ንግግር ያደረጉት ሚስተር ጆርጅ አሱሬ (በስተቀኝ)።

የአዉደ ጥናቱ ተሣታፊዎች በከፊል

በአዉደ ጥናቱ የቀረቡት 24 የምርምር ጽሑፎች የሚከተሉት ናቸዉ።

ሀ) አግሮኢኮሎጂና የዘር ሲስተም

1. Ecology and farming systems በታመነ መኮንን

2. Tef seed system and input supply በዶክተር አበበ አጥላዉ

ለ) ጄኔቲክስና ብሪዲንግ

3. Taxonomy, origin and genetic resources በዶክተር ሀብቴ ጅፋር

4. Genetics በዶክተር ሰለሞን ጫንያለዉ

5. Breeding በዶክተር ክበበዉ አሰፋ

ሐ) ጄኖሚክስና ባዮቴክኖሎጂ

6.Molecular breeding በዶክተር ደጀኔ ግርማ

7. Biotechnology በዶክተር እንዳለ ገብሬ

8. Genomics በዶክተር ደጀኔ ግርማ

9. Progress and prospects of genome editing in tef improvement በምትኩ አስፋዉ

የአዉደ ጥናቱ ተሣታፊዎች በከፊል

መ) አፈርና ሰብል እንክብካቤ

10. Morphology and anatomy በታራ ዋይግት

11. Physiology በዶክተር ዘሪሁን ታደለ

12. Agronomy በዶክተር አልማዝ መሠረት

13. Soil fertility management በዶክተር ይፍሩ አበራ

14. Water management በአሸብር ኃይሌ

15. Mechanization በደረጀ አለሙ

16. Response of tef grain physico-chemical properties to soil and meteorological factors በአንተነህ አበዋ

ሠ) ሰብል ጥበቃ

17. Weed management በአቶ ረዘነ ፍስሃዬ

18. Disease management በአሸናፊ ገመቹ

19. Insect pest management በዶክተር ጠብቀዉ ዳምጤ

ረ) ሶሺዮ ኢኮኖሚክስ እና ኢክስቴንሽን

20. Food value በዶክተር ወርቅነህ አበበ

21. Feed value በተክለዮሃንስ ብርሃኑ

22. Economics of Tef በዶክተር ስጦታዉ ፈረደ

23. Tef technology transfer በዶክተር ኤልያስ ዘርፉ

24. Tef value chain በዶክተር ባርት ሚንተን

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ጥቅምት 23፣ 2012 ዓ.ም. (November 3, 2019)

አስተያየት ያስቀምጡ