ግብርናችንን ለማዘመን፤ ስለ ግብርናችን የጻፉልን

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

ስለ ግብርናችን የጻፉልን

ሰለ አንድ ማንኛዉም ነገር ግንዛቤ እንዲኖረን በቅድሚያ የምናደርገዉ መሥራት ባቀድነው መስክ ላይ ቀደም ብሎ የተሠራ ነገር ካለ መረጃ ማሰባሰብ ነዉ። የምናሰባስበዉ መረጃም ባብዘኛዉ ሊገኝ የሚችለዉ ቀድም ብሎ ከታተሙ የተለያዩ ጽሑፎች ነው። እነዚህ ጽሑፎች ለአንባቢያን የሚቀርቡበት መንገድም እንዲሁ ይለያያል። ኦሪጂናል የሆኑ የምርምር ዉጤቶች ባብዘኛዉ የሚቀርቡት ወቅታቸዉን ጠብቀዉ በሚታተሙ ጆርናል በሚባሉ የህትመት ዓይነቶች ነዉ። ከዚህ ዉጭ ሌሎች ጽሁፎች በመጽሐፍ፣ በሪፖርት ወይም በሌላ መልክ ሊቀርቡ ይችላሉ።

ስለ ኢትዮጵያ የሚጠቅሱ የጆርናል ጽሑፎች ባለፉት አንድ መቶ ዓመታት (ከ1900 እስከ ዛሬ መስከረም 18 ቀን 2012) ስንት ይሆናሉ ብዬ ዌብ ኦፍ ሳይንስ የሚለዉን ድህረ ገጽ ስጠይቅ 26,886 ናቸዉ የሚል መልስ አገኘዉ። ሌላዉ ጥያቄዬ ኢትዮጵያና እርሻ የሚሉትን ቃላት አጣምሮ የያዙ ጽሑፎች የሚለዉ ሲሆን የዚህ መልሱም 1,024 ብቻ እንደሆኑ ነዉ። ከዚሁ በተጓዳኝ ኢትዮጵያና ደን የሚሉ ቃላትን አጣምረዉ የያዙ 1,169 ሲሆኑ ኢትዮጵያና ጤና የሚሉትን ቃላት አጣምረዉ የያዙ ደግሞ 6,418 ናቸዉ። በርግጥ በራሴም ግምገማ በጤናዉ መስክ ኢትዮጵያን በተመለከተ በርካታ የጆርናል ጽሑፎች ይታተማሉ። ይህ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ ቃላትን በጣምራ በመጠቀም የሚገኘዉ ዉጤት ትክክለኛ ቁጥርን ሊያሳይ አይችልም። ምክንያቱም በተጻፈዉ ጽሑፍ ውስጥ ሁለቱ ቃላት ባንድነት ላይታዩ ሰለሚችሉ ነዉ። ቢሆንም ጥሩ አመላካች ሊሆን ይችላል።

የሀገራችን ግብርናን የሚመለከቱ የተውሰኑ መጽሐፍት ይኖራሉ። ነገር ግን ሁሉንም በተማከለ ሥፍራ ማግኘት አዳጋች ሊሆን ይችላል። ምክንያቱም በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚሰባሰቡበት ቤተ መጽሐፍ ስለሌለ ነዉ። ከዚህ በታች የተጠቀሱት ጥቂት መጽሐፍት ለማስረጃ እንዲሆኑ ብዬ ያቀረብኳቸዉ ናቸዉ እንጂ በርካታ መጽሐፍት ሊጠቀሱ ይችላሉ።

  • Agricultural Systems in Ethiopia by Westphal E. (1975)
  • Agricultural Transformation in Ethiopia: State Policy and Smallholder Farming by Beyene A. (2018)
  • Coffee Atlas of Ethiopia by Davis A, Wilkinson T, Challa ZK, Baena S, Gole TW, Moat J. (2018)
  • Food and Agriculture in Ethiopia: Progress and Policy Challenges by Dorosh PA, Rashids S. Eds. (2012)
  • Foreign Direct Investment in Large-Scale Agriculture in Africa: Economic, Social and Environmental Sustainability in Ethiopia by Persson AGM. (2019)
  • Guidelines for Development Agents on Soil Conservation in Ethiopia by Author Hurni H. (1986)
  • People of the Plow: an Agricultural History of Ethiopia, 1800–1990 by McCann JC. (1995)
  • Plant Genetic Resources of Ethiopia by Engels JMM, Hawkes JG, Worede M. (1991)

የዛሬዉ ጽሑፌ የሚያተኩረዉ በቅርቡ በዶክተር ጌታቸዉ ድሪባ የታተመዉና ከፍተኛ የሚዲያ ሽፋን ስላገኘዉ መጽሐፍ ነዉ። የመጽሐፉ ርዕስ ‘Overcoming Agricultural and Food Crisis in Ethiopia: Institutional Evolution and the Path to Agricultural Transformation’ የሚባል ሲሆን የታተመዉም ከአንድ ዓመት በፊት እ.ኤ.አ. በ2018 ነዉ። መጽሐፉ በ11 ምዕራፎች የተከፈለና በአጠቃላይ 417 ገጾች ያሉት ነዉ። እኔም መጽሐፉን በኦንላይን ገዝቼ እያነበብኩ ነኝ። መጽሐፉን በተመለከተ የተጻፉ የግምገማ ጽሑፎችና እንዲሁም በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ደራሲዉ የሰጡትን ቃለ መጠይቅም ለማንበብ ችያለሁ።

ጸሐፊዉ የመጀመሪያ ድግሪያቸዉን ከሀረማያ ዩኒቨርሲቲ፣ የማስትሬት ዲግሪያቸዉን ጀርመርን ሀገር ከሚገኘዉ የዶርትሙንድ ዩኒቨርሲቲ በመቀጠልም ፒ ኤች ዲ እንግሊዝ ሀገር ከሚገኘዉ የኢስት አንግሊያ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል። በሙያቸዉም የእርሻ ኢኮኖሚክስት ናቸዉ። በሥራ ልምድም በኢትዮጵያ ዉስጥም ሆነ ከኢትዮጵያ ውጭ በተለያዩ መንግሥታዊም ሆነ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ለበርካታ ዓመታት ሠርተዋል። እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስም ዋና ጽሕፈት ቤቱ ሮም በሚገኘዉ የዓለም ምግብ ድርጅት ዉስጥ በከፍተኛ ኃላፊነት ይሠሩ ነበር።


ዶክተር ጌታቸዉ የተወለዱት ከአሰላ ከተማ በቅርበት በምትገኘዉና ከታዋቂዉ የጭላሎ ተራራ ሥር ካለችዉ ዶሻ በምትባል መንደር ነዉ። የዶሻ መንደርም የአሰላ ብቅል ፋብሪካና የቁሉምሳ እርሻ ምርምር ማዕከል ካሉበት በ20 ኪ.ሜ. የሚገኝ ቦታ ነዉ። በመጽሐፋቸዉ መግቢያ ላይም ዶክተር ጌታቸዉ የዚህ የተወለዱበትን አካባቢ የግብርና ለውጥን ይተርካሉ። ይህ አካባቢም በኢትዮጵያ ዉስጥ ዘመናዊ የግብርና አሠራርን ካገኙ ሥፍራዎች ቀደምትነቱን ይይዛል። በመጀመሪያ ካዱ በመቀጠልም አርዱ በሚል መጠሪያ ከስዊዲን መንግሥት ጋር በተደርገ ትብብር ሠፊ የልማት ሥራ የተከናወበት ሥፍራ ነዉ። ዶክተር ጌታቸዉ በመጽሐፋቸዉ ውስጥ የሀገራችን ግብርና በሶስቱ መንግሥታት ያደረገዉን ዕድገት ወይም ለዉጥ በዝርዝር ያቀርባሉ።

በዛሬዉ ጽሁፌ በመጽሐፉ ላይ ያለኝን የራሴን ግምገማ ለማቅረብ ሳይሆን ባጋጣሚ መጽሐፉን ላላያችሁ አንብባችሁ የራሳችሁን ግንዛቤ እንድትወስዱ ብዬ ነዉ። ከመጽሐፉ በተጨማሪ ተሾመ ሁንዱማ እና ሰላም ኃይለሚካኤል የተባሉት ጸሐፊያን ጃኑዋሪ 6፣ 2019 ኢትዮጵያ ኦብዘርቨር ላይ ስለ መጽሐፉ ያደረጉትን ግምገማና በሪፖርተር ላይ የታተመዉን የደራሲዉን ቃለመጠይቅ ማንበብ ጠቃሚ ነዉ።

ማጠቃለያ፤ ስለ ሀገራችን ግብርና የሚያወሳ ብዙ መረጃ በሌለበት ዉድ ጊዜያቸዉን ሰዉተዉ ስለሀገራችን ግብርና አመጣጥም ሆነ ሂደት እንዲሁም ለወደፊት ያለዉን ተስፋ የጻፉልን ከፍተኛ ምስጋና ይገባቸዋል። ምክንያቱም የድርሻቸዉን አበርክተዋልና ነዉ። የዛሬ ጽሑፌን የማበቃዉ የሪፖርት ጋዜጠኛ የሆነዉ ብርሃኑ ፍቃዴ ለዶክተር ጌታቸዉ ካደረገላቸዉ ቃለ መጠይቅ ዉስጥ መጽሐፉን ለመጻፍ ምን እንዳነሳሳቸው ሲጠይቃቸዉ በመለሱት መልስ ነዉ። “መጽሐፉን ለመጻፍ ያነሳሳኝ በዉስጤ ያለዉ ቁጭት ነዉ። በሥራ ምክንያት በበርካታ ሀገራት ለመጓዝ ዕድል አግኝቻለዉ። የሀገራቱን የግብርና ዕድገትም በቅርበት ለማየት ችያለዉ። የኛ ሀገር ግብርና ግን ገና ብዙ ይቀረዋል።” ትርጉሙን ቃል በቃ አልተረጎምኩትም።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መስከረም 18፣ 2012 ዓ.ም. (September 29, 2019)

አስተያየት ያስቀምጡ