ግብርናችንን ለማዘመን፤ የአየር ንብረት ለውጥን እንግታ!!!

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የአየር ንብረት ለውጥን እንግታ!!!

በምሥሉ የሚታየዉ የዓለምን ህዝብ ያነቃነቀችዉ የ16 ዓመቷ ግሬታ ቱንበርግ ሰሞኑን ከቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ጋር በተገናኘችበት ወቅት ነዉ። የምሥሉ ምንጭ

ከሁለት ቀናት በፊት ዓርብ መስከረም 9፣ 2012 (እ. ኤ. አ. ሴፕቴምቤር 20, 2019) በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የአለማችን ወጣቶች ድምጻቸዉን ለማሰማት አደባባይ ወጥተዉ ነበር። ወደ አደባባይ ለመዉጣት ያበቃቸዉም የአየር ንብረት ለውጥ በማድረስ ላይ ያለዉንና በቅርቡም ያደርሳል ተብሎ የሚጠበቀዉን መጥፎ ክስተቶች እንዲታደጉላቸዉ በመንግስቶቻቸዉ ላይ ተጽእኖ ለማድረግ ነዉ። በራሳቸዉ ሀገራትም ብቻ ሳይወሰኑ ሰሞኑን በኒዉዮርክ በሚደረገዉ የተባበሩት መንግስታት ጉባኤ ላይም የአየር ንብረት ለዉጥ ከፍተኛ ትኩረት እንዲያገኝ ለማድረግ ነዉ። ከላይ እንደገለጽኩት በዚህ ከፍተኛ ሰላማዊ ሰልፍ በተለየ ሁኔታ የተሳተፉት ወጣቶች ናቸዉ። ምክንያቱም የአየር ንብረት ለዉጥ ከፍተኛ ተጽእኖ የሚያደርሰዉ በእነርሱ ላይ እንደሆነ ሰለተረዱና ይህንንም ለህብረተሰቡ ለማስገንዘብ ነዉ። በተጨማሪም ይህ የአየር ንብረት ለውጥ ሊያደርስ ይችላል ተብሎ የሚጠበቅዉን መጥፎ ክስተትም ለመግታት ዕርምጃ እንዲወሰድ ጥሪ ለማድርግ ነዉ።

ይህ አዉስትራሊያ፣ አዉሮፓ፣ አፍሪካ፣ እንዲሁም ሰሜንና ደቡብ አሜሪካ በሚገኙ 150 ሀገራት የተደረገዉ የተቃዉሞ ሰልፍ የተመራዉ ግሬታ ቱንበርግ በምትባል ወጣት አክቲቪት ነዉ። ስለዚች ቆራጥ ወጣት የስዊድን ዜጋ ከዚህ በፊት የአየር ንብረት ለዉጥን አስመልክቶ በጻፍኳቸዉ ብሎጎች ውስጥ ህብረተሰቡ ምን ይላል በሚል ሰኔ 16 ቀን 2011 በከተብኩት ጽሑፍ ለማሳየት ሞክሬአለሁ። በሀገሯ ስዊዲንና በርካታ የአውሮፓ ከተሞች እየተዘዋወረች ካደረገቻቸዉ ንግግሮች በተጨማሪ ሰሞኑን በአሜሪካ የተወካዮች ምክር ቤት በመገኘት የአየር ንብረት ለውጥን ለመግታት አስተዋጾ እንዲያደርጉ አሳስባለች። ወደ አሜሪካ የተጓዘችዉም ከአንድ ወር በፊት ሲሆን 15 ቀናት በፈጀ የጀልባ ጉዞ ሲሆን ይህም በጸሐይ ብርሃን በመታገዝ የሚነዳ ነዉ። በመሆኑም ለጤናችን ጎጂ የሆነዉ ካርቦን ወደ ከባቢያችን እንዳይረጭ ታሳቢ በማድረግ ነዉ።

ከሁለት ቀናት በፊት በተደረጉት ሰላማዊ ሰልፎች ላይ በርካታ መሳጭ መፈክሮችም ተይዘዉ ነበር። በየሀገራቱም ከፍተኛ የሚዲያ ሽፋን አግኝተዉ ነበር። ከነዚህ ውስጥ ‘ሌላ ዓለም የለንም’ የሚለዉ ልብ የሚነካ ነዉ። ከአፍሪካ ሀገራት ዉስጥ የተሟላ መረጃ ባይኖረኝም በደቡብ አፍሪካና ኬኒያ የሚገኙ ወጣቶችም ወደ አደባባይ ውጥተዉ ድምጻቸዉን አሰምተዋል።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ መስከረም 11፣ 2012 ዓ.ም. (September 22, 2019)

አስተያየት ያስቀምጡ