በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤
ክብረ ወሰን በዛፍ ተከላ!!
የኢትዮጵያ መንግሥት በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ባደረጉት ጥሪ መሠረትና ህብረተሰቡ ባደረገዉ ከፍተኛ ተሳትፎ ሐምሌ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. በአንድ ጀምበር ብቻ 353,633,660 የዛፍ ችግኞች በሀገሪቱ ሊተከሉ ችለዋል። ይህ የዛፍ ተከላ ቆጠራም የተከናወነዉ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተመርኩዞ በመሆኑ ከፍተኛ ተቀባይነት አለዉ። ለዚሁ ሲባል የግብርና፣ ኢኖቬሽንና ሌሎች የሚመለከታቸዉ መሥሪያ ቤቶች በተቀናጀ ሁኔታ እንደተሣተፉበት ተከላዉ በተደረገበት ቀን ምሽት ከተሰጠዉ ጋዜጣዊ መረጃ መረዳት ችያለዉ።
ኢትዮጵያኖች በሙሉ ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ጨምሮ እንዲሁም በሀገሪቱ የሚገኙ የዉጭ ሀገር ዲፕሎማቶች የተሳተፉበት ይህ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በሀገሪቱ ከተደረጉትና ሀብረተሰቡን በአንድ ወቅት በጋራ በማሳተፍ ከተሰሩ ሥራዎች ሁሉ ግዙፉ ነዉ ማለት ይቻላል። ስለዚህ ለዚህ የልማትና በጎ ሥራ ለህዝቡ ጥሪ ላቀረቡት ለጠቅላይ ሚኒስትሩና እንዲሁም መርሀ ግብሩ ተፈጻሚነት እንዲያገኝ ከፍተኛ ርብርብ ላደረጉት በተለያየ ደረጃ ለሚገኙ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም ሆኑ ግለሰቦች ከፍተኛ ምሥጋና ሊደርሳቸዉ ይገባል።
ከዛፍ ወይም ደን ጋር ተዛማች የሆኑ በቅርቡ የጻፍኳቸዉ ሶስት ብሎጎች ከዚህ በታች በተገለጹት ሊንኮች ማግኘት ይቻላል።
1ኛ) የአየር ንብረት ለውጥ — በደናችን (ዛፎቻችን)፣
2ኛ፟) የአየር ንብረት ለውጥ — የካርቦን ገበያ፣ ታክስና ፈንድ፣ እና
3ኛ) ባህር ዛፍ ጠቀመን ወይስ መጠመጠን? የሚሉት ናቸዉ።
በነዚሁ ጽሑፎኝ እንደተገለጸዉ ዛፍ ከሚያስገኝልን በርካታ ጥቅሞች በተጨማሪ ለአየር ንብረት ለዉጥ መባባስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርገው ካርቦንዳይኦክሳይድ ወደ ከባቢያችን እንዳያፈተልክና ለጉዳት እንዳይዳርገን አምቆ በመያዝ ይጠቅመናል።ከአንድ ዛፍ ጠቅላላ ክብደቱ ዉስጥ ግማሹን የሚይዘዉ ካርቦን ነዉ። በዚሁ መሠረት 12 ዓመት የሆነውና 600 ኪ.ግ. የሚከብድ ዛፍ በዉስጡ 859 ኪ.ግ. ካርቦንዳይኦክሳይድ አምቆ የሚይዝ ሲሆን በአንድ ሄክታር ላይ ያለ ደን (በአንድ ሄክታር 650 ዛፍ ቢኖር) በ12 ዓመት 0.56 ሚሊዮን ኪ.ግ. ካርቦንዳይኦክሳይድ አምቆ ይዟል ማለት ነዉ። ከላይ በተገለጸዉ ስሌት መሠረት በሐምሌ 22 ቀን ብቻ በኢትዮጵያ የተተከሉት 353,633,660 ችግኞች በ544,051 ሄክታር መሬት ላይ ያረፉ ቢሆን በሚቀጥሉት 12 ዓመታት በጠቅላላዉ 304.7 ቢሊዮን ኪ.ግ. ካርቦንዳይኦክሳይድ አምቀዉ ይይዛሉ ማለት ነዉ። ስለዚህ የአየር ንብረት ለዉጥን በመግታት ከፍተኛ ድርሻ ያበረክታሉ ማለት ነዉ።
ይህ ከፍተኛ የህዝብ ተሳትፎ የነበረዉ የዛፍ ተከላ በሀገር ዉስጥ ካለዉ ሚዲያ ባልተናነሰ መልኩ በውጭ የሚገኙ ታዋቂ ሚዲያዎች ከፍተኛ ሽፋን ሰጥተዋል። የዚህን ዜና ከነዚህ ሚዲያዎች የሰሙ ወይም ያነበቡ የሥራ ባልደረቦቼም አድናቆት በተሞላበት መልኩ ጠይቀዉኛል። በወቅቱ ዜናዉን ከዘገቡት ዉስጥ ጥቂቶቹ ከዚህ በታች ተገልጸዋል። የጽሑፉን ሙሉ ይዘት ርዕሱን በመጫን ማግኘት ይቻላል።
CNN: Ethiopia plants more than 350 million trees in 12 hours
New York Times: Ethiopia Plants More Than 200 Million Trees in 1 Day
Washington Post: Ethiopia plants more than 200 million trees in 1 day
BBC: Ethiopia ‘breaks’ tree-planting record to tackle climate change
The Guardian: Ethiopia plants 250 million trees in a day to help tackle climate crisis
Bloomberg: Ethiopia plants 350 million trees in one day to combat drought
Africa news: Ethiopia breaks world record for tree planting in a single day
Metro: Ethiopia breaks record by planting 350,000,000 trees in a day to fight climate change
The Hill: Ethiopia plants more than 350 million tree seedlings in one day to fight climate change
Almariam (አልማሪያም)፣ ታዋቂዉ የህግ ባለሙያና የካሊፎርኒያ ስቴት ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር Ode to 4 Billion Tree Saplings by the River Ghion (Ethiopia)
ሰሞኑን ባርሴሎና ነበርኩ። ደራርቱ የዛሬ 27 ዓመት በ10 000 ሜትር ድል የተቀዳጀችበት የ1992ቱ የባርሴሎና ኦሎምፒክ ሥፍራ ማየት አለብኝ ብዬ በመጀመሪያው ቀን ቦታዉን ለማግኘት አዳጋች ቢሆንብኝም በማግስቱ አግኝቼዋለዉ። የመሮጫ ትራኩንና ሙዚየሙን እንዲሁም ለማሸነፍ በተቃረበችበት ጊዜ የነበረዉን ሁኔታ የሚያሳዩ ምሥሎች ከዚህ በታች ማየት ይቻላል።

ከላይ የሚታየዉ ደራርቱ የሮጠችበት ትራክና ስታዲየም ነዉ።

ይህ በባርሴሎና የሚገኘዉ የኦሎምፒክ ሙዚየም የተሰየመዉ በታዋቂዉ አንቶኒዮ ሳማራንች ነዉ። ሳማራንች በባርሴሎና የተወለዱ ሲሆን የኢንተርናሽናል ኦሎምፒክ ኮሚቴ ፕሬዘዳንት በመሆን ለ21 ዓመታት ያገለገሉ እጅግ ተወዳጅ መሪ ነበሩ። በሙዚየሙ ዉስጥ እስከ 2000 የሲድኒ ኦሎምፒክ የነበሩ አበበ ቢቂላን ጨምሮ የታዋቂ አትሌቶች ምስልና ቪዲዮ ይገኛል።

ከላይ የሚታየዉ ምሥል የሚያሳየዉ ደራርቱ ድል ልትቀዳጅ በተቃረበችበት ወቅት የነበረዉን ሁኔታ ነዉ።
በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።
ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ነሐሴ 1፣ 2011 ዓ.ም. (August 7, 2019)