ግብርናችንን ለማዘመን፤ የአየር ንብረት ለውጥ — ህብረተሰቡ ምን ይላል?

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የአየር ንብረት ለውጥ — ህብረተሰቡ ምን ይላል?

በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች በተለይም በአዉሮፓ ያሉ አክቲቪስቶች በአየር ንብረት ለዉጥ ምክንያት ሰለሚከሰተዉ አስደንጋጭ ሁኔታ እጅግ ስላሳሰባቸዉ መንግሥታቸዉ ወይም አህጉሩ ጠበቅ ያለ አቋም እንዲወስዱ በየጊዜዉ እየወተወቷቸዉ ነው። በዚህ ብቻም ሳይወሰኑ የተቃውሞ ሰልፎችንም ጭምር በማደራጀት ድምፃቸዉን ያሰማሉ። ለአየር ንብረት መለወጥ እንደ ማስረጃ የሚያቀርቡት የአየርና የባህር ሙቀት መጨመር፣ የዝናም እጥረት ወይም ድርቅ መባባስ፣ የጎርፍ መብዛት፣ የግሪንሃዉስ ጋዝ መጠን መጨመር፣ የበረዶ ክምችት መመናመን፣ የባህር ወለል ከፍ ማለት እና የባህር ዉሃ ወደ አሲዳማነት መቀየር ናቸዉ።

ከዚህ ተያይዞ ያንዲት የስዊዲን ሀገር ወጣት ተማሪን አስተዋጽኦ መጥቀስ ያስፈልጋል። ስሟ ግሬታ ቱንበርግ ይባላል። በዓለም ዙሪያ የአየር ንብረት ለውጥን በሚመለከት ለህብረትሰቡ ግንዛቤ ለመስጠትና መንግሥታትም እርምጃ እንዲወስዱ ለማሳሰብ የወሰነች ናት። ተቃዉሞዋን የጀመረችዉ የዛሬ አንድ ዓመት (በኦግስት 20፣ 2018) ነዉ። በወቅቱ የዘጠነኛ ከፍል ተማሪ የነበረችዉ የ15 ዓመቷ ግሬታ ትምህርቷን አቋርጣ የሀገሪቱ ፓርላማ ህንጻ ፊት ብቻዋን ሆና ተቃዉሞዋን ማሰማት ጀመረች። ቤተሰቦቿ ትምህርቷን እንዳትተዉ ቢማጸኗትም እንዲሁም የትምህርት ቤት ጓደኞቿ ባይቀላቅሏትም መፈክሯን ይዛ የበረዶዉ፣ የዝናቡና የፀሐዩ መፈራረቅ ሳይበግራት ለወራት ፓርላማዉ ፊት ትቀመጥ ነበር። በዚህ ቆራጥ ዓላማዋና ድርጊቷ የዓለምን ትኩረት ሳበች። ይህች ወጣትም በተለያዩ መድረኮች ንግግር እንድታደርግ መጋበዝ ጀመረች። ከነዚህ ወስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰዉ የዓለማችን ታዋቂ ሰዎች የሚጋበዙበት በያመቱ በዳቮስ ስዊዘርላንድ የሚካሄደው የዓለም ኢኮኖሚክ ፎረም ነዉ። ከዚህ ሌላ በተለያዩ መድረኮችም ከሀገር መሪዎች ጭምር የመገናኘትና ድምጿን የማሰማት ዕድል አግኝታለች። የአየር ንብረት ለዉጥን በተመለከተ በሚደረጉ ስብሰባዎች ላይ ትጋበዛለች። በርካታ ሽልማቶችንና ዕውቅናን ለማግኘት በቅታለች። የኖብል ተሸላሚ እንድትሆንም ጥሪ እየቀረበ ነዉ። ይህች ወጣት አይሮፕላን ከፍተኛ መጠን ያለዉ ካርቦንዳይኦክሳይድ ወደ ከባቢያችን ሰለሚረጭ ማዕቀብ አድርጋበታለች። ምንም እንኳ ጉዞዋ አንዳንድ ጊዜ ረዥም ጊዜ ቢወስድባትም ካንድ ሀገር ወደ ሌላ የምትጓዘዉ በባቡር ነዉ። ሌላዉ የግሬታ ባህርይ ራሷን ወደ ቬጋን መቀየሯ ነዉ። በዚሁ መሠረት ማንኛዉም ከእንስሳ የሚገኝ ነገር (እንደ ሥጋ፣ ወተት፣ አይብ፣ እንቁላል) አፏ አጠገብ አይደርሱም። ምከንያቱም እንሰሳዎቻችን ከፍተኛ የሆነ የግሪን ሀዉስ ጋስ ወደ አካባቢችን ስለሚረጩ ነዉ። ይህ በሷ ብቻ የተጀመረዉ የአየር ንብረት የተማሪዎች ተቃዉሞ ተስፋፍቶ ከሶስት ወራት በፊት (በማርች 15፣ 2019) በ112 ሀገራት ያሉ በግምት 1.5 ሚሊዮን የሚሆኑ ተማሪዎች እንዲሁም ከአንድ ወር በፊት (ሜይ 24፣ 2019) በ125 ሀገራት ያሉ ትማሪዎች ሊሳተፉበት ችለዋል።

የአየር ንብረቴ (My Climate) የሚለዉና በስዊዘርላንድ ትልቁ በሆነችው በዙሪክ ከተማ የተመሠረተው ይህ ፋዉንዴሽን https://www.myclimate.org/compensate/today/ ትንሽ የምለዉ አለኝ። ይህ ፋዉንዴሽን የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ በርካታ መረጃዎች በእንግሊዘኛና ጀርመንኛ ቋንቋዎች ያቀርባል። በተለይ በኑሮአችን ዉስጥ ምን ያህል ካርቦንዳይኦክሳይድ በከባቢያችን እንደምንረጭ ያሳየናል። ለምሳሌ በአይሮፕላን ስንበር፣ በመኪና ስንሄድ ወይም በመርከብ ስንቀዝፍ የምናቃጥለዉን የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን አስልቶ ይሰጠናል። ለምሳሌ እኔ ካለሁበት ሀገር ወደ ወደ ኢትዮጵያ የደርሶ መልስ በረራ ለማካሄድ ከጄኔቫ በቀጥታ ወደ አዲስ አበባ በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚደረገዉ ጉዞ አጭሩ ነዉ። ይህም ወደ 10400 ኪሎ ሜትር እንደሚሆን ይገመታል። በዚህ ድህረ ገጽ ስሌት መሠረት በረራዬ በኢኮኖሚ ከፍል ከሆነ የሚቃጠለዉ የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን 1.9 ቶን ሲሆን በቢዝነስ ክፍል ደግሞ 3.7 ቶን እና ፈርስት ክላስ በሚባለዉ ደግሞ 5.8 ቶን ነዉ። ስለዚህ ባንድ ጉዞ ለዓመቱ የተመደበልንን አንድ ቶን የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን አለፍን ማለት ነዉ። በተመሣሣይ መልኩ ከአዲስ አበባ ወደ ድሬዳዋ በአይሮፕላን ደርሶ መልስ የሚጓዝ ሰዉ 0.25 ቶን የሚያቃጥል ሲሆን የዓመት ኮታዉን በአራት ጉዞዎች ያጠናቅቃል ማለት ነው።

የዚህ ፋዉንዴሽን ሌላው ዓላማ ከኮታችን በላይ የምንጠቀመዉን የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን በገንዘብ መልክ እንድንከፍልና የአየር ንብረትን ለመታደግ በሚደረጉ የልማት ሥራዎች ላይ በተለይም በመልማት ላይ ባሉ ሀገሮች እንዲዉል ማድረግ ነዉ። በዚሁ መሠረት ከላይ በተጠቀሰዉ የጄኔቫ – አዲስ አበባ ጉዞ ከኮታ በላይ ለተጠቀሙት ትርፍ ካርቦንዳይኦክሳይድ የኢኮኖሚ ክፍል ተጓዥ 55.00 ዶላር፣ የቢዝነስ ክፍል 106.00 ዶላር እና የፈርስት ክላስ 165.00 ዶላር እንዲከፍል ይጠበቅበታል።

በዚሁ የአየር ንብረት ለዉጥ ምክንያት ሊከሰት የሚችለዉን የካርቦንዳይኦክሳይድ መጠን ለህብረትሰቡ ግንዛቤ ለመስጠት ይኸዉ ፋዉንዴሽን ሰሞኑን ግዙፍ ባሉኖችን በትልልቅ ከተሞች አስቀምጧል። ከነዚህ ወስጥ እኔ በምኖርበት የበርን ከተማ የከተማዉ ማዕከል በሆነ ሥፍራ የተቀመጠመዉን ከዚህ በታች በምሥሉ ማየት ይቻላል።

በምሥሉ የሚታየዉ የግሪን ሃዉስ ጋዝ አካል ስለሆነዉ ካርቦንዳይኦክሳይድ ሲሆን ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለመስጠት በየከተማዉ ይህን የመሰለ ግዙፍ ባሎን በማስቀመጥ ነዉ። በባሎኑም ላይ የተጻፈዉ “የአየር ንብረትን ለመግታት የሚያስችል የካርቦን ኮታህ ወይም ኮታሽ የተወሰነ ነዉ። ዛሬ የት ነህ ወይም ነሽ” ይላል። በባሎኑ ላይ እንደሚታየዉ የአንድ ሰዉ የዓመቱ ኮታ አንድ ቶን ካርቦንዳይኦክሳይድ ነዉ። ፎቶ፤ ዘሪሁን ታደለ፣ በርን ከተማ ሰኔ 12, 2011 (June 19, 2019)

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ሰኔ 16፤ 2011 ዓ.ም.

አስተያየት ያስቀምጡ