ግብርናችንን ለማዘመን፤ የአየር ንብረት ለውጥ — በጤናችን

በዚህ ብሎግ ሥር ግብርናን በተመለከተ በተለያዩ ርዕሶች በተከታታይ አጫጭር ጽሁፎች አቀርባለሁ። እነዚህ ጽሑፎች የሚያተኩሩት እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ህዝባችን በሚተዳደርበትና የኔም የሙያ መስኬ በሆነዉ ግብርና ላይ የራሴን አስተዋጽዖ ለማበርከት ነዉ። የዛሬዉ እነሆ፤

የአየር ንብረት ለውጥ — በጤናችን

እንደሌላዉ ሴክተር ሁሉ የአየር ንብረት ለዉጥ በጤናችን ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማደረስ ላይ ይገኛል። የተባበሩት መንግሥታት የዓለም ጤና ድርጅት በቅርቡ ባወጣዉ ሪፖርት መሠረት እ.ኤ.አ. ከ2030 እስከ 2050 ባሉት 20 ዓመታት ውስጥ ከአየር ንብረት ለዉጥ ጋር በተያያዘ በያመቱ 250 ሺህ ሰዉ እንደሚሞት ይጠበቃል። ዝርዝሩን ከዚህ በታች ባለዉ ምሥል ማየት ይቻላል።

ምሥሉ የሚያሳየዉ እ.ኤ.አ. ከ2030 እስከ 2050 ባሉት ዓመታት ዉስጥ በአየር ንብረት ለዉጥ ምክንያት በያመቱ በዓለማችን ሊደርስ የሚችለዉን የሞት አደጋ ነው። የተባበሩት መንግሥታት የዓለም ጤና ድርጅት ሪፖርትን በመመርኮዝ ነዉ ምሥሉን የሳልኩት።

በሪፖርቱ መሠረት ለከፋ አደጋ የሚጋለጡት በአብዘኛዉ በመልማት ላይ ያሉ አገሮች ናቸዉ። ምክንያቱም ሊያጋጥም የሚችለዉን አደጋ ለመቋቋም ያላቸዉ ዝግጁነት አነስተኛ ሰለሆነ ነዉ። ቢሆንም ጥቃቱ ድንገተኛና አጣዳፊ ከሆነ የለሙ ሀገሮችም ከጥቃቱ ሊያመልጡ አይችሉም። ለዚህ እንደምሳሌ የሚጠቀሰዉ የዛሬ 16 ዓመት እ.ኤ.አ. በ2003 በአዉሮፓ በከፍተኛ የአየር ሙቀት ምክንያት እስከ 70 ሺህ የሚደርሱ ሰዎች የሞቱበት ክስተት ነዉ። በተለይ ለዚህ ጥቃት የተጋለጡት አረጋዊያን ነበሩ።

የአየር ንብረት ለዉጥ በጤናችን ላይ በቅጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ተጽእኖ ያደርጋል። ይህንኑ በግልጽ ለማሳየት ቀደም ብሎ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽንና ሌሎች ድርጅቶች ትብብር የወጣዉን የፖሊሲ መግለጫ ተርጉሜ ከዚህ በታች ባለዉ ሠንጠረዥ አቅርቤዋለሁ።

ከላይ የተገለጸዉ መግለጫ እንደሚያሳየዉ በአፍሪካ የተመጣጠነ ምግብ ባለማግኘት በያመቱ 1.7 ሚሊዮን ሰዉ ለሞት ይዳረጋል። የተለያዩ የተቅማጥና እንዲሁም የወባ በሽታዎችም የበርካታ ዜጎችን ሕይወት ይቀጥፋሉ።

ሀገራችንን በተመለከተ ከአየር ንብረት ለዉጥ ጋር ተያይዞ ስለጤናቸን ሲወራ በብዛት የሚነገረዉ ስለ ወባ ነዉ። ምክንያቱም ከዛሬ 20 እና 30 ዓመታት በፊት የወባ በሽታ ባልነበረበት ከፍተኛ ቦታዎች በመዛመት ላይ በመገኘቱ ነዉ። ለዚህ እንደ ምከንያት የሚጠቀሰዉ እነዚህ ከፍታ ቦታዎች የአየር ሙቀታቸዉ መጨመር ነዉ። በዚህ አጋጣሚ መግለጽ የሚያስፈልገዉ የወባ በሽታ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በብዙ ሀገራት ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል። በዓለማችን በየዓመቱ ወደ ግማሽ ሚሊዮን የሚሆን ሰዉ በወባ ይሞታል። እንደሚታወቀዉ ሁሉ ለወባ በሽታ መንስኤ የሆነዉን ረቂቅ ተዉሃስ በማስተላልፍ የምትረዳዉ በተለምዶ ቢምቢ የምንላት ነፍስ ናት። ቢምቢዋ ወዳጅ መስላ ጠጋ ብላ ወባ ከያዘዉ ሰው ያመጣችዉን ረቂቅ ህዋስ እንደ ከትባት ትወገናለች።

አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያሳዩት በቢምቢዎች የመጠቃት ዕድላችን ከሰዉ ሰዉ ይለያያል። በዚሁ መሠረት ቢቢዎችን ወደ እኛ የሚስባቸዉ ከሰዉነታችን የሚወጣው ሽታና የምንተነፍሰዉ ካርቦን ዳይኦክሳይድ ነዉ። ለኔ ሌሎች ምከንያቶችም ያሉ ይመስለኛል። ለዚህ እንደ ምሳሌ የምጠቅሰዉ ራሴን ነዉ። በመካከለኛዉ አዋሽ በሚገኘዉ በወረር እርሻ ምርምር ማዕከል በቆየሁባቸዉ ከሶስት ዓመታት በላይ ጓደኞቼና የሥራ ባልደረቦቼ በተደጋጋሚ በወባ ሲያዙ እኔ ባጋጣሚም ሆነ በሌላ ምከንያት አንድም ቀን ሊያዝ አልቻልኩም። በአካባቢዉ ግን እጅግ ከፍተኛ የሆነ የወባ በሽታ ነበር።

ይህንኑ በኛ ግቢ ዉስጥ ወደ ነበረችዉ ክሊኒክ ከሚጎርፈዉ የሰዉ ብዛት መገንዘብ ይቻላል። ለህክምና የመጣዉ ሰዉ ደሙን ከሰጠ በኋላ ዉጤቱ ሲነገረዉ የሚጠብቀዉ ቫይቫክስ ወይም ፈልሲፓረም መባልን ነዉ። ምንም እንኳ በከፍተኛ ህመም ዉስጥ ቢሆኑም ቫይቫክስ ሲባሉ ፈገግ ይላሉ። ምክንያቱም እንደ ፈልሲፓረም ፋታ ሳይሰጥ ለክፉ አይሰጥምና ነዉ።

በዚህ አጋጥሚ መጥቀስ የምፈልገዉ ለጥጥ ለቀማ ከሌላ አካባቢ የሚመጡ በርካታ ዜጎቻንን የዚሁ የወባ ሰለባ መሆናቸዉ ነዉ። የአንድ ወጣት አሟሟት ግን እስካሁን ከፊቴ አይጠፋም። ቤቴ ወደ ክሊኒኩ መወሰጃ መንገድ ላይ ነበር። አንድ ቀን በግቢያችን ውስጥ በሥራ የነበሩ ሰዎች የሆነ ሰዉ መንገድ ላይ እንደወደቀ ነገሩን። ሄደን ስናየዉ ዕድሜዉ በግምት 20 ዓመት የሚሆን ወጣት በህይወት የለም። ። እንደሚመስለኝ ወደ ክሊኒክ የሚያደርሰዉ ሰው በማጣቱ ቢያንስ ከ500 ሜትር በላይ በራሱ ተራምዶ ክሊኒኩ ለመድረስ 50 ሜትር ሲቀረዉ ወደቆ በዚያዉ ቀረ፤ ማንም ሳይደርስለት ሞቶ ተገኘ። ያቺ ፈልሲፓረምን የያዘችዉ ክፉ ቢምቢ አግኝታዉ ነዉ ለዚህ ያበቃችዉ። እኛም በአካባቢዉ ያሉ ሰዎችን አስተባብረን ቀበርነዉ። የዚህ ወጣት መርዶ ለዘመዶቹ እንኳ እንዳይላክ መታወቂያ ኪሱ ዉስጥ አልተገኘም ነበር።

እዚህ ላይ መታወቅ የሚገባዉ ወባ የሚያሰታላልፉም ሆነ የማያስተላልፉ ቢምቢዎች አሉ። ኤክስፐርቶቹ የቢምቢዋን የአቋቋም ሁኔታ በማየት የቷ ዓይነት ቢምቢ እንደሆነች በርግጠኝነት ይናገራሉ። ስለዚህ በቢምቢ ተነከስን ማለት ወባ ያዘን ማለት አይደለም።

በሀገራችን የተደረገ ሌላ ጥናት እንደሚያሳየዉ ከአየር ንብረት ለዉጥ ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ በሽታዎች እየጨመሩ በመምጣት ላይ እንደሆኑ ነዉ። እነዚህ ለህመምም ሆነ ለሞት የሚዳርጉት በሽታዎች እንደ ዉሃ ወለድ በሽታዎች፣ በአየር ብክለት የሚመጡ የመተንፈሻ አካል ህመሞች እና ሜኒንጂቲሥን ያካትታሉ።

በሚቀጥለዉ በሌላ ጽሑፍ እስክንገናኝ መልካሙን እመኛለሁ።

ዘሪሁን ታደለ፣ ከበርን ከተማ ስዊዘርላንድ፣ ሰኔ 15፤ 2011 ዓ.ም.

አስተያየት ያስቀምጡ